የኮከቡ ቦክሰኛ የመሐመድ አሊ ስንብት
ዓርብ፣ ሰኔ 3 2008ከሳምንት በፊት በ74 ዓመቱ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየዉ ቦክሰኛ በኖረባት ኬንታኪ ከተማ በሀገሩ ሰዓት አቆጣጠር ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት አንስቶ የተጀመረዉ የጸሎት ሥርዓት ከተፈጸመ በኋላ አስከሬኑ ወደሚያርፍበት ስፍራ ተወሰዳል። ለሦስት ተከታታይ ጊዜያት በከባድ ክብደት ቦክስ የዓለም ሻምፒዮና ለነበረዉ ታዋቂ ሰዉ በሺዎች የተገመቱ አድናቂዎቹ በተገኙበት የስንብትና የመታሰቢያ ሥርዓት ተከናዉኖለታል። በስፍራዉ ከተገኙት አንዱ፤
«ከዲትሮይት አንስተን፤ ሚቺጋን እንዲሁም ከሲንሲናቲ እና ካንሳስ ድረስ ነዉ የመጣነዉ፤ አሁን አንድ ሰዓት ተኩል ገደማ ይሆነናል ከደረስን።»
አስከሬኑ ታጅቦ የልጅነት ጊዜዉን ባሳለፈባት ከተማ ዋና ዋና ጎዳናዎች እንዲያልፍ የሚደረግ ሲሆን በሀገሩ አቆጣጠር ከቀኑ ስምንት ሰዓት ላይ ግብዓተ መሬት እንደሚፈጸም ዘገባዎች ያመለክታሉ። በስንብት ሥርዓቱ ላይ ከተገኙት መካከልም የቀድሞዉ የአሜሪካን ፕሬዝደንት ቢል ክሊንተን፤ እንዲሁም የዮርዳኖሱ ንጉሥ አብደላ እና የቱርክ ፕሬዝደንት ራቺብ ታይብ ኤርዶኻን ተጠቅሰዋል።
እንዲያም ሆኖ የቱርኩ ፕሬዝደንት በቀብሩ ሥርዓት ላይ ሳይገኙ ወደ ሀገራቸዉ እንደተመለሱ ነዉ የተገለጸዉ። ዶቼ ቬለ በፌስ ቡክ ገጹ ላይ ስለመሀመድ አሊ ከአድማጮች ጋር ባካሄደዉ ዉይይት ታዋቂ ቦክሰኛ ብቻ ሳይሆን የሰዉ ልጅ እኩልነት መብት ተሟጋች ነበር በማለት ብዙዎች አድናቆታቸዉን ገልጸዉለታል።
ሸዋዬ ለገሠ
ኂሩት መለሰ