የኬንያ ተከሳሽ ፖለቲከኞች
ረቡዕ፣ ግንቦት 28 2005ዓለም አቀፉ የወንጀለኞች መቅጫ ፍርድ ቤት (ICC) በኬንያ ፖለቲከኞች ላይ የተመሠረተዉን ክስ እዚያዉ ኬንያ አለያም ታንዛኒያ ዉስጥ ለማድመጥ ማቀዱን ለተበዳዮች የሚከራከሩ የሕግ ባለሙያዎች ተቃወሙት።የዓለም አቀፍ የሕግ አስከባሪዎች ኮሚሽን ባልደረቦች እንደሚሉት ተከሳሾቹ ኬንያ ወይም ታንዛኒያ ከተዳኙ የኬንያ መንግሥት እና ባለሥልጣናት በፍርዱ ሒደት፥በተለይም በምስክሮች ላይ ተፅዕኖ ሊያሳርፉ ይችላሉ።ዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት በኬንያ ፕሬዝዳትና በምክትላቸዉ ላይ የተመሠረተዉን ክስ አፍሪቃ ዉስጥ ለመስማት ማቀዱን ያስታወቀዉ ከአፍሪቃ መሪዎች ጠንካራ ትችት ከተሠነዘረበት በኋላ መሆኑ ነዉ።
ኬንያ ዉስጥ ታሕሳስ 2000 የተደረገዉ ምርጫ አወዛጋቢ ዉጤት ሕይወት፥ አካል፥ ሐብት ንብረት ባጠፋ ድቀት ማሳረጉ ተራዉን ኬንያዊ በጎሳ፥ የኬንያ ፖለቲከኞችን በሥልጣን፥ የኬንያ መንግሥት እና ዓለም አቀፉን ፍርድ ቤት (ICC በእንግሊዝኛ ምሕፃሩ) በፍርድ ሒደት እንዳወዛገበ ኬንያ ሌላ ምርጫ አደረገች-ዘንድሮ የካቲት።ዘ-ሔግ ኔዘርላድስ የሚያስችለዉ ፍርድ ቤት አቃቤ ሕግ በሰብአዊነት ላይ በተፈፀመ ጥፋት ከከሰሳቸዉ ተጠርጣሪዎች ሁለቱ ደግሞ የኬንያ ፕሬዝዳት እና ምክትል ፕሬዝዳት ሆኑ።
የያኔዎቹ ተቀናቃኞች የዛሬዎቹ ወዳጅ ፖለቲከኞች ኡሑሩ ኬንያታ እና ዊሊያም ሩቶ ትላልቁን ሥልጣን ከያዙ ወዲሕ ክሱ የአፍሪቃ ሕብረትንም ከዉዝግቡ ዶሏል።ሰሞኑን አዲስ አበባ የተሰብስበዉ የነበሩት የአፍሪቃ መሪዎች ዓለም አቀፉን ፍርድ ቤት በዘረኝነት ወቅሰዉ፥ክሱ በኬንያ ፍርድ ቤቶች እንዲታይ ጠይቀዉ ነበር።ዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት ወቀሳዉንም፥ ጥያቄዉንም አጣጥሎ ነበር የነቀፈዉ።ይሑንና የፍርድ ቤቱ ዳኞች አንድም ኬንያ ዓለያም ታንዛኒያ ለማስቻል ማቀዳቸዉን ከትናንት በስቲያ ማስታወቃቸዉ ፍርድ ቤታቸዉ ለአፍሪቃ ሕብረት ተፅዕኖ ባይንበረከክ ሸብረክ-ማለቱን ጠቋሚ ነዉ።
3አዲሱ ዕቅድ ግን አዲስ ተቃዉሞ ገጥሞታል።ተቃዋሚዉ።ለተበዳዮች የሚቆረቆረዉ ዓለም አቀፍ የሕግ-ባለሙያዎች ኮሚሽ ነዉ፥ (ICJ በእንግሊዝኛ ምሕፃሩ።) የኮሚሽኑ ባልደረባ ወይዘሮ ስቴላ ንዲራንጉ እንደሚሉት ፍርድ ቤቱ ኬንያ ወይም ታንዛኒያ የሚያስችል ከሆነ በከፍተኛዉ የመንግሥት ሥልጣን ላይ የሚገኙት ተከሳሾች የፍርዱን ሒደት በቀላሉ ተፅዕኖ ሳያርፉበታል።ምስክሮች ደፍረዉ አይናገሩምም።እና ፍትሕ-በእሳቸዉ እምነት ይዛባል።
«የምንፈልገዉ የሁሉንም ወገን ጉዳይ የሚያካትት ፍትሕን ነዉ።ለተከሳሾች ጉዳይ ብቻ ትኩረት የሚሠጥ መሆን የለበትም።እንደሚመስለኝ ፍርድ ቤቱ ለ(ኬንያ) በቀረበ ሥፍራ የሚያስችል ከሆነ ለተከሳሾቹ ብቻ እንጂ ለሰለቦቹ እና ፍትሕን ለሚደግፈዉ የኬንያ ሕዝብ የሚፈይደዉ የለም።»
የችሎቱ ሥፍራ ታቀደ እንጂ አልተወሰነም።ፍርድ ቤቱ በምክትል ፕሬዝዳት ዊሊያም ሩቶ እና በአንድ ራዲዮ ጣቢያ ሐላፊ በጆሽዋ አራፕ ሳንግ ላይ የተመሠረተዉን ክስ ለማድመጥ ለሐምሌ ይዞት የነበረዉን ቀጠሮ ወደ መስከረም ገፍቶታል።ፍርድ ቤቱ ታንዛኒያ ወይም ኬንያ ያስችል መባሉን የሚቃወሙት ንዲራንጉ ቀጠሮዉ መራዘሙን ግን ደግፈዉታል።
«አሁን ለመስከረም አዲስ ቀን ተቆርጧል።ያንን መጠበቁ ጥሩ ነዉ።ምክንያቱም ሚዛናዊ ብይን ለማግኘት ዝግጅት ያስፈልጋል።የቀኑ መራዘም ሁሉም ወገኖች የሚጠቅማቸዉን መረጃ ለማሠባሰብ ጠቃሚ ነዉ።ብዙ ሰዎች አይናገሩትም እንጂ አዳዲስ መረጃዎችም ተገኝተዋል።»
የአፍሪቃ ሕብረት ጥያቄ ቀኑ ይራዘም፥ ወይም የችሎቱ ሥፍራ-ይቀየር አይደለም።ተከሳሾች በሐገራቸዉ በኬንያ ፍርድ ቤቶች ይዳኙ-እንጂ።የሕግ ባለሙዋ የአፍሪቃ ሕብረትን ጥያቄ-በጥያቄ ነዉ-ያጣጣሉት።
«የአፍሪቃ ሕብረት ጉባኤ ዋና ዉሳኔ እንደሆነዉ፥-የኬንያ ፍርድ ቤቶች ጉዳዩን ይመልከቱ ቢባል እንኳን ፍርድ ቤቶቹ እስካሁን የሠሩትን ማየት ያስፈልጋል።ምን ሠሩ? ICC የሚመለከታቸዉ ሰዎስት ጉዳዮች ናቸዉ።ከምርጫዉ በሕዋላ ከደረሰዉ ጥፋት ከፍተኛነትና ከተጠርታሪዎች ብዛት ጋር ሲነፃፀር በጣም ትንሽ ነዉ።የኬንያ ፍርድ ቤቶች አቅሙ አላቸዉ ከተባለ ሌሎቹን ጉዳዮች ለመዳኘት እስካሁን ያደረጉት ምንድነዉ? አቅማቸዉን በገቢር ማሳየታቸዉን ልናዉቅ ይገባልም።»
ዉዝግብ ክርክሩ ቀጥሏል።ዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት በፕሬዝዳት ኡሑሩ ኬንያታ ላይ የተመሠረተዉን ክስ ሐምሌ መጀመሪያ ላይ ለመስማት የያዘዉን ቀጠሮ ግን እስካሁን አልተቀየረም።
ነጋሽ መሐመድ
ተክሌ የኋላ