የኬሪና የጀርመን ባለሥልጣናት ዉይይት
ማክሰኞ፣ የካቲት 19 2005
የዩናይትድ ስቴትስና የአዉሮጳ ሕብረት ነፃ የንግድ ቀጠና እንዲመሠርቱ የጀርመንና የዩናይትድ ስቴትስ ባለሥልጣናት በጋራ ጠየቁ።የዩናይትድ ስቴትሱ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ጆን ኬሪ ዛሬ በርሊን ዉስጥ ከጀርመንዋ መራሒተ መንግሥትና ከጀርመኑ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ጋር በጉዳዩ ላይ ተነጋግረዋል።ኬሪ መራሒተ-መንግሥት አንጌላ ሜርክልንና ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ጊዶ ቨስተርቬለን ካነጋገሩ በሕዋላ እንዳሉት በአዉሮጳና በዩናይትድ ስቴትስ መሐል ነፃ የንግድ ቀጠና መመሠረት የፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ ሁለተኛ ዘመነ-ሥልጣን ልዩ ትኩረት ነዉ።ኬሪ ሐገራቸዉ ከጀርመን ጋር ያላትን የንግድ ትብብር ይበልጥ ማጠናቀር እንደምትሻም አስታዉቀዋል።
«ጀርመን ከአዉሮጳ ሐገራት ትልቋ የንግድ ተሻራኪያችን ናት።ሥራ የሚፈጥር፤ ከዚሕ የበለጠ ንግድና ኢንቨስትመት እንዲኖር እንፈልጋለን።ለአሜሪካዉያን፥ ለጀርመኖች እና ለመላዉ አዉሮጳዉያን ሥራ የሚፈጥር።»የጀርመኑ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ጊዶ ቬስተርቨለ በበኩላቸዉ የኬሪን ጉብኝት የአዉሮጳና የአሜሪካ ወዳጅነት የመጠናከሩ ምልክት ብለዉታል።
«የአሜሪካ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሥልጣን በያዙ ማግሥት ጀርመንና አዉሮጳን መጎብኘታቸዉ ለአትላንቲክ ማዶ ለማዶዉ ወዳጅነት (መጠናከር) ግልፅ ምልክት ነዉ።
የአሜሪካዉ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ከጀርመን አስተናጋጆቻቸዉ ጋር የአዉሮጳ የምጣኔ ሐብት ኪሳራን፥ የሶሪያዉን ጦርነት፥ የኢራንን የኑክሌር ዉዝግብ እና የእስራኤል-ፍልስጤሞችንም ጉዳይ አንስተዉ መክረዋል።ኬሪ እዚያዉ በርሊን ዉስጥ ከሩሲያዉ አቻቸዉ ከሰርጌይ ላቫሮቭ ጋርም በተለይ የሶሪያዉን ጦርነት አስተዉ ተነጋግረዋል።ከአሜሪካዊ ዲፕሎማት የሚወለዱት ጆን ኬሪ በ1950ዎቹ የልጅነት ጊዚያቸዉን በርሊን ነዉ ያሳለፉት።የያኔ ትዝታቸዉን ዛሬ ለበርሊን ወጣቶች ተርከዉላቸዋል።
ነጋሽ መሐመድ
አርያም ተክሌ