የከተሞች ፎረም በጅግጅጋ እየተከበረ ነው
ቅዳሜ፣ የካቲት 9 2011“መደመር ለሀገራችን ከተሞች ብልፅግና” በሚል መሪ ሀሳብ ዛሬ በጅግጅጋ ከተማ የተጀመረውን የኢትዮጵያ ከተሞች ፎረም በይፋ የከፈቱት የኢፌድሪ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ የምንገኝበት ጊዜ ያሉብንን ችግሮች በፍጥነትና በጥራት ከመስራት ውጭ አማራጭ የሌለበት ነው ብለዋል።
ፕሬዝዳንቷ ያሉብንን ችግሮች ለመፍታት ጊዜ እንደሌለን በመገንዘብ ኢትዮጵያዊ አንድነታችንን አጠናክረን መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል በንግግራቸው።
ክብርት ፕሬዝዳንት ሳሕለወርቅ ከረዥም ጊዜ በፊት እንደሚያውቋት በገለፇት ጅግጅጋ ከተማ ባዩት ሁለንተናዊ ለውጥ መደሰታቸውን ጠቁመው ፎረሙን በይፋ ከፍተዋል።
የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚንስቴር ሚንስትር አቶ ጃንጥራር አባይ በበኩላቸው ፎረሙ በሀገሪቱ በቁጥር እያደጉ የሚገኙ ከተሞች ልምድ የሚለዋወጡበት ከመሆን ባለፈ በሚንስቴሩ የተቀመጠውን ራዕይ ለማሳካት ይረዳል ብለዋል ፡፡
የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፋ መሀመድ በስነ ስርዓቱ ላይ እንዳሉት 8ኛው ከተሞች ፎረም በዓል ህዝቡ በክልሉ በነበረው አምባገነን ስርኣት ሲፈፀሙ የነበሩ የአስተዳደር ፣ የመልካም አስተዳደር በደልና ሌሎች ችግሮች ታግሎ በለወጠበት ማግስት የመጣ ድርብ ድል ነው።
አቶ ሙስጠፌ በቅርቡ ተፈጥሮ የነበረውን ጠባሳ በመሻር ህዝቡ የሚታወቅበትን ደግ፣ እንግዳ ተቀባይና ሀይማኖተኛነቱን የሚያሳይበት እንደሚሆንም አረጋግጠዋል።
አንድ መቶ ስልሳ ዘጠኝ የኢትዮጵ ከተሞችና ከተጎራባች ሀገራት የጅቡቲ ፣ የሶማሌ ላንድ ከተሞች ሀርጌሳ እና በርበራ በዚሁ ፎረም ላይ ተሳታፊ ሆነዋል ፡፡ የተሌዩ የፌደራልና የክለል ስራ ሀላፊዎች በተገኙበት የተጀመረው ፎረም በኤግዚብሽን በፓናል ውይይት እና መሰል ዝግጅቶች እስከ መጪው ሀሙስ የሚቀጥል ይሆናል።
መሳይ ተክሉ
እሸቴ በቀለ