የኦብነግ ወታደሮች በሶማሌላንድ መከበብ
ማክሰኞ፣ መስከረም 4 2003ማስታወቂያ
የኦጋዴን ነጻ አውጪ ግንባር አባላት እንደሆኑ የታመኑ 250 ታጣቂዎችን በሶማሌላንድ፤ በጅቡቲና በሶማሌላንድ ድንበር ላይ በሚገኝ የሶማሌላንድ ግዛት ውስጥ መክበቧንና ማባረሯን አስታወቀች። የሶማሌላንድ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሞሀመድ ዩሱፍ አዋሌ እንደገለጹት ድንበር አቋርጠው የገቡት ታጣቂዎች በተሰነዘረባቸው ጥቃት ሸሽተው ወደኢትዮዽያ ግዛት ሄደዋል። በዚህ ጥቃት 50 ታጣቂዎች በሶማሌላንድ ኃይል መገደላቸውን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አስታውቀዋል። እነዚህ ታጣቂዎች የኦጋዴን ብሄራዊ ነጻ አውጪ ግንባር አባላት ለመሆናቸው ትተው ከሄዷቸው የተለያዩ ማስረጃዎች እንደተረጋገጠ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። የኦጋዴን ብሄራዊ ነጻ አውጪ ግንባር ክሱን የፈጠራ ሲል አስተባብሏል። የግንባሩ ቃል አቀባይ አብዱራህማን መህዲ የሶማሌላንድ አዲሱ መንግስት ከኢትዮዽያ መንግስት ጋር የገጠመውን ችግር ለመሸፈን ሲል የፈጠረው ክስ ነው ብለዋል።
መሳይ መኮንን
ነጋሽ መሐመድ