የኦሮሚያ ፖሊስ በክልሉ ሰላምና ፀጥታን ለማረጋገጥ ወሰድኩ ያለው ዕርምጃ
ረቡዕ፣ ኅዳር 9 2013ማስታወቂያ
በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ጉሊሶ ወረዳ ንጽሃን ላይ ያነጣጠረ የጅምላ ግድያ ከተወሰደ ወዲህ መንግስት በወሰደው አፀፋዊ እርምጃ ባለፉት ሁለት ሳምንታት በአከባቢው 142 የሸማቂ ኃይል አባላት ላይ የግድያ እና የማቁሰል አደጋ ሲደርስ 132 ታጣቂዎችን ደግሞ በቁጥጥር ስር በማዋል ትጥቅ ለማስፈታት መቻሉን የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ገለፀ፡፡
የፖሊስ ኮሚሽኑ ኮሚሽነር ጄነራል አራርሳ መርዳሳ ዛሬ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ እንዳሉት በጉሊሶ የ34 ንጹሃን ዜጎችን ህይወት ከቀጠፈውና በመቶዎች የሚቆጠሩትን ካፈናለው ጥቃት ወዲህ ለሸማቂው ኃይል ድጋፍን በማድረግ የተጠረጠሩት ተጨማሪ 1,341 ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ስር በማዋል መዝገባቸው እየታየ ይገኛል፡፡ ከዚህ ውስጥ ደግሞ 104 ያህሉ የህወሓት አባላት ሆነው መገኘታቸው ነው የተገለጸው፡፡
ኮሚሽነሩ አክለው እንዳሉት በርካታ የጦር መሳሪያ እና ገንዘብ በኦፐሬሽኑ በቁጥጥር ስር ለማዋል ተችሏል፡፡
በዚህም "ኦነግ ሸነ ነው" ያሉት ሸማቂ ቡድን "ከህወሓት" ጋር መስራቱን ዳግም አረጋግጠናል ያሉት ኮሚሽነር አራርሳ መርዳሳ፤ በትግራይ ክልል የፌዴራል መንግስት እርምጃ መውሰድ ከጀመረ ወዲህ በኦሮሚያ አንጻራዊ ሰላም ተስተውሏልም ነው ያሉት፡፡
ስዩም ጌቱ
ኂሩት መለሰ