የኢትዮጵያ የምርጫ ህግ ማሻሻያ
እሑድ፣ ኅዳር 23 2011በኢትዮጵያ በተያዘው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት፣ሀገር አቀፍ ምርጫ ለማካሄድ አንድ ዓመት ከ6 ወር ያህል ጊዜ ነው የቀረው። ምርጫውን ዴሞክራሲያዊ እና ፍትሀዊ ለማድረግ ይረዳሉ የተባሉ እርምጃዎች በመወስድ ላይ ናቸው። ከመካከላቸው በምርጫ ቦርድ አወቃቀር እና የምርጫ ህግ ማሻሻያ ላይ የሚካሄደው ውይይት አንዱ ነው። የምርጫው አስፈጻሚ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድም ከሳምንት በፊት አዲስ ሰብሳቢ ተሰይሞለታል። የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐብይ አህመድ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች መሪዎች ጋር ባለፈው ማክሰኞ ባካሄዱት ውይይት ቀጣዩን ምርጫ ነጻ እና ፍትሀዊ ለማድረግ ያስፈልጋሉ የሚባሉ ለውጦች ላይ መክረዋል። የምርጫ ህግ እና አፈጻጸም ላይ ይታያሉ የሚባሉ ጉድለቶችን ለማሟላት ፣መሻሻል ያለባቸውንም ለማስተካከል የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ቢደረጉም ምርጫው በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ መካሄድ መቻል አለመቻሉ እያከራከረ ነው። ከውጭ በቅርቡ ወደ ሀገር ውስጥ የገቡትን ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ጨምሮ በሀገር ውስጥ ከሚንቀሳቀሱም የተወሰኑት ጊዜው አጭር ነው የሚል መከራከያ እያቀረቡ ነው። ምርጫው በታቀደው መሠረት እንዲካሄድ የሚደግፉ ደግሞ መዘግየቱ አደጋ ሊኖረው ይችላል ሲሉ እያስጠነቀቁ ነው። የኢትዮጵያ የምርጫ ህግ ማሻሻያ እና የ2012 ዓም ምርጫ የዛሬው እንወያይ ትኩረት ነው። በዚህ ውይይት ላይ የሚሳተፉ 3 እንግዶችን ጋብዘናል። እነርሱም ዶክተር መረራ ጉዲና የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ በአጭሩ መድረክ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል እና የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ሊቀመንበር፣ አቶ ኤፍሬም ማዴቦ የአርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነት እና ለዴሞክራሲ ንቅናቄ የፖለቲካ ዘርፍ ሃላፊ እንዲሁም አቶ ሰሎሞን ጎሹ የህግ ባለሞያ እና በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የህግ መምህር ናቸው።
ኂሩት መለሰ
ልደት አበበ