የአዲሱ ጠ/ሚ ሹመት መፅደቅ
ዓርብ፣ መስከረም 11 2005
አዲሱ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስርት አቶ ሐይለማርያም ደሳለኝ መንግሥታቸዉ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓትን ለማጠናከር፥ የሠብአዊ መብትን ለማስከበር እንደሚጥር አስታወቁ።ባለፈዉ ወር ያረፉትን አንጋፋዉን የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር አቶ መለስ ዜናዊን የተኩት አቶ ሐይለ ማርያም ዛሬ ከሐገሪቱ ምክር ቤት ፊት ቃላ መሐላ ፈፅመዉ የጠቅላይ ሚንስትርነቱን ሥልጣን ተረክበዋል። የትምሕርት ሚንስትር አቶ ደመቀ መኮንንም ዛሬ የምክትል ጠቅላይ ሚንስትርነቱን ሥልጣን ይዘዋል።ጠቅላይ ሚንስትር ሐይለማርያም የጠቅላይ ሚንስትርነቱን ሥልጣን ከተረከቡ በሕዋላ ባደረጉት ንግግር መንግሥታቸዉ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓትን ለማጠናከርና ሠብአዊ መብትን ለማስከበር አበክሮ ይጥራል።ጠቅላይ ሚንስትሩ እክለዉ እንዳሉት መንግሥታቸዉ ከተለያዩ የዲሞክራሲ፥ የመብት ተሟጋቾች ተቋማት እና ከተቃዋሚዎች ጋር ለመተባበርም ዝግጁ ነዉ።
አቶ ሐይለ ማርያም ከ2003 ጀምሮ የኢትዮጵያ ምክትል ጠቅላይ ሚንስትርና የዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሆነዉ ሠርተዋል።አቶ ደመቀ ደግሞ ከሁለት ሺሕ ጀምሮ በትምሕርት ሚንስትርነት አገልግለዋል።የኢትዮጵያ ገዢ ፓርቲ ኢሕአዴግ ሁለቱን ፖለቲከኞች የፓርቲዉ ሊቀመንበርና ምክትል ሊቀመንበር፥ የሐገሪቱ ጠቅላይ ሚንስትርና ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር አድርጎ የመረጠዉ ባለፈዉ ቅዳሜ ነበር።አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ቀላል የማይባል ኃላፊነትና ፈተና እንደሚጠብቃቸዉ ከወዲሁ ዘገባዎች ቢገልፁም አቶ ኃይለማርያም የቀድሞዉ ጠቅላይ ሚኒስትር የጀመሩትን አጠናክረዉ ለመቀጠል መዘጋጀታቸዉን በመጀመሪያዉ ንግግራቸዉ ዛሬ ግልፅ አድርገዋል።
ዮሐንስ ገብረእግዚአብሔር
ሸዋዬ ለገሠ
አርያም ተክሌ