የአውሮጳ ኅብረት ርዳታ ለአፍሪቃ ኅብረት
ረቡዕ፣ መጋቢት 22 1996ማስታወቂያ
መንበሩ በአዲስ አበባ የሚገኘው የአፍሪቃ ኅብረት በአህጉሩ ውዝግብ በበዛባቸው አካባቢዎች የሰላም ማስከበሩን ሚና እንዲይዝ ዓለም አቀፍ ግፊት ቢያርፍበትም፡ ይኸው ጥረቱ በገንዘብ እጥረት የተነሣ እክል እንደገጠመው ነው የሚገኘው። አፍሪቃውያን መሪዎች በርዋንዳ እአአ በ 1984 ዓም የታየው ዓይነት የጎሣ ጭፍጨፋ ድጋሚ እንዳይነሣ ለማከላከል ቁርጥ ፍላጎት እንዳላቸው አረጋግጠዋል። መሪዎቹ በአህጉሩ የርስበርስ ጦርነትና የጎሣ ጭፍጨፋዎች በሚነሡበት ጊዜ ጣልቃ ገብቶ ርምጃ የሚወስድ አንድ የበርካታ ሀገሮች ጦር ጓድ ለማቋቋም የተስማሙት ባለፈው የካቲት ነበር። ጓዱ እአአ እስከ 2005 ዓም ድረስ በአምስት የአህጉሩ አካባቢዎች እንደሚሠማራ፡ እስከ 2010 ዓ ዓም ድረስ ደግሞ አፍሪቃ አቀፍ ጓድ እንደሚሆንና በተለይ ከደቡብ አፍሪቃ፡ ናይጀሪያ፡ ኬንያ እና ግብፅ የተውጣጡ ወደ አሥራ አምስት ሺህ የሚጠጉ ወታደሮች እንደሚኖሩት የኅብረቱ ምንጮች ገልፀዋል።