የአክሱም ሐውልት አደጋ ላይ ነው
ረቡዕ፣ የካቲት 6 2011የአክሱም ሐውልት አደጋ ላይ መሆኑ የአካባቢው ነዋሪዎችና በሐወልቶቹ ላይ ጥናት የሰሩ ባለሙያዎች ገለፁ፡፡ በተለይ ቁጥር ሶስት ተብሎ የሚታወቀው ለዘመናት ከቦታው ሳይንቀሳቀስ የቆየው የአክሱም ሐውልት አሁን ወደ ሰሜን ምስራቅ አቅጣጫ መዝመሙን ጥናት ያደረጉ የኦርኪዮሎጂ ምሁር ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ ቅርስ ጥበቃ ባለስልጣን በበኩሉ የጥገና ስራዎች ለማካሄድ ቅድመ ዝግጅት እያደረገ መሆኑ ገልፅዋል፡፡
የአክሱም ስልጣኔ አሻራዎች የሆኑት የአክሱም ሐወልቶች በተፈጥሮአዊና ሰው ሰራሽ አጋጣሚ አደጋዎች ሲያስተናገዱ መቆየታቸው ይነገራል፡፡ ከቅርብ ግዜ ወዲህ ግን በተለይም ቁጥር ሶስት ተብሎ የሚታወቀው ሐወልት በከፋ ሁኔታ እየተጎዳ መሆኑ ተገልፅዋል፡፡ በሐወልቱ ላይ ጥናት የሰሩት በመቐለ ዩኒቨርሲቲ የአርኪዮሎጂ መምህር የሆኑት ሕሉፍ በርሀ "ከጣሊያን የመጣው የአክሱም ሐወልት ሲተከል ቁጥር ሶስት ተብሎ በሚታወቀው ነባሩ የቆመ ሐወልት ላይ ጉዳት ደርሷል" ይላሉ፡፡
በተደረገው ጥናትም ወደ ሰሜን ምስራቅ አቅጣጫ በዜሮ ነጥብ ሁለት ሶስት ዲግሪ ዘሞ እንደሚታይ ምሁሩ ገልፀዋል፡፡ የአክሱም ከተማ ባህልና ቱሪዝም ፅሕፈት ቤት ሐላፊ አቶ ገብረመድህን ፍፁምብርሃን በበኩላቸው የአደጋው መጠን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ ነው ሲሉ ለDW ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ ቅርስ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ዮናስ ደስታ በበኩላቸው "በሐወልቱ ላይ ጥገና ለማካሄድ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ሲከወኑ ነበር" በማለት በቅርቡ ጥገና ይጀመራል ብለዋል፡፡ ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ ከመቀሌ በዚህ ላይ ያተኮረ ዘገባ አዘጋጅቷል።
ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ
ኂሩት መለሰ
ነጋሽ መሐመድ