የአሸባብ ጥቃት ዒላማ ኬንያ
ረቡዕ፣ ሰኔ 20 2004ለእሁዱ ጥቃት እስካሁን ኃላፊነቱን የወደሰ ወገን ባይኖርም፡ ለጥቃቱ በኬንያ ላይ ተመሳሳይ ጥቃት እንደሚጥል በተደጋጋሚ ዛቻ ያሰማው የሶማልያ አክራሪ ሙሥሊሞች ቡድን የአሸባብ ስራ እንደሚሆን መጠርጠሩን የኬንያ መንግሥት ገልጾዋል።
ብዙ ሕዝብ የአውሮጳ እግር ኳስ ዋንጫ ግጥሚያ በቴሌቪዝን ይከታተል በነበረበት ቡና ቤት ላይ የተጣለውን የቦምብ ጥቃት የአሸባብ ደጋፊዎች ሳይፈጽሙት እንዳልቀሩ የጠረጠረው የኬንያ መንግሥት ተጨማሪ ጥቃት ሊጣል እንደሚችል አስጠንቅቆዋል። ኬንያ ባለፈው ጥቅምት ወር በሶማልያ የሽግግር መንግሥት አንጻር የሚታገሉትን የአሸባብ ተዋጊዎችን ለመደምሰስ ወታደሮችዋን ወደ ደቡብ ሶማልያ ከላከች ወዲህ በርካታ የእጅ ቦምብ ጥቃት ሰለባ ሆናለች። በተለይ ኬንያ አሁን አሸባብን ከኪስማዩ ወደብ ከተማ ለማባረር ግዙፍ ዘመቻ ለማካሄድ ዝግጅት የጀመረችበት ድርጊት ለጥቃት ሊያጋልጣት ይችላል በሚል ስጋት በሀገሪቱ ስልታዊ ከተሞች ጥበቃውን ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑን የኬንያ ፖሊስ ምክትል ቃል አቀባይ ቻርልስ ሶዊኖ አስታውቀዋል።
« በወቅቱ ትልቅ የጥቃት ዒላማ ሆነናል። እና እንደተለመደው ጥበቃውን፡ የመረጃ ልውውጥ ዘዴአችንን አጠናክረናል። የሽብር ተግባር ለመጣል በማቀዱ ተግባር ላይ ሊሳተፉ ይችላሉ ብለን የምንጠረጥራቸውን በጥብቅ እየተከታተልን እንገኛል። »
የኬንያ ፖሊስ ምክትል ቃል አቀባይ በተጨማሪ እንዳመለከቱት፣ በቁጥጥር የዋሉት ተጠርጣሪዎች ምርመራ አሁንም ቀጥሎዋል።
ለጥቃቱ ምናልባት የሞምባሳ ወደብ አካባቢን ከኬንያ ለመገንጠል የሚታገለው የሞምባሳ ሬፓብሊካን ምክር ቤት የተሰኘው ቡድን ተጠያቂው ሊሆን እንደሚችል አንዳንድ ያልተረጋገጡ ዘገባዎች አመልክተዋል። ይሁንና፡ በናይሮቢ የሚገኘው የአንድ የፖለቲካ ተመራማሪ ተቋም ተንታኝ ሼክ አብዲ ሳማድ ሼክ አብዲ ዋሀድ ለእሁዱ የፍንዳታ ጥቃት ቡድኑ ተጠያቂ ሊሆን እንደማይችል ገልጸዋል።
« አሸባብ ነው። ምክንያቱም ካሁን በፊትም በናይሮቢ ተመሳሳይ ርምጃ ወስደዋል። በሰሜናዊ ኬንያ አድርገውታል፣ በሞምባሳም። »
ኬንያ በሀገርዋ ላይ ኬንያውያን ላይ ነው ጦርነት ቢያወጅም፡ የኬንያ ፀጥታ ኃይላት እና የኬንያ ሕዝብ በአሸባብ አንፃር ባንድነት እየሰሩ ያለበት ሁኔታ ሀገሪቱን ከከፋ ጉዳት እንደጠበቃት የኬንያ ባለሥልጣናት ገልጸዋል። የኬንያ ጦር በቅርቡ ሊያካሂደው ያሰበው ዘመቻም የኬንያን ፀጥታ አስተማማኝ ሊያደርግ እንደሚችል የፖለቲካ ተንታኙ ሼክ አብዲ ሳማድ ሼክ አብዲ ዋሀድ ይገምታሉ።
« የኬንያ መከላከያ ሠራዊት በአሸባብ ቁጥጥር ያለችውን በደቡብ ሶማልያ የምትገኘውን የኪስማዩ ወደብን ለመያዝ ተቃርቦዋል። ይህ ዘመቻው ከተሳካ አሸባብ የደቀነው ስጋት ሰማንያ ከመቶው ያህል ይቀነሳል። እና ይህ ኬንያውያን ሀገራቸውን ከሶማልያ ጋ የሚያዋስነውን ድንበር በቀላሉ እንዲቆጣጠሩ ያስችላቸዋል ማለት ነው። »
የሞምባሳው ጥቃት ሊጣል አንድ ቀን ሲቀረው የዩኤስ አሜሪካ ኤምባሲ አሸባሪዎች በከተማይቱ ጥቃት ሊጥሉ እንደሚችሉ ማስጠንቀቂያ አቅርቦ ነበር። የኬንያ የቱሪዝም መሥሪኣ ቤቶች ባለሥልጣናት ግን ያሜሪካውያኑን ማስጠንቀቂያ ቱሪስቶች ወደሀገራቸው እንዳይመጡ የሚያደርግ የኤኮኖሚ አሻጥር ነው በሚል በማውገዝ ኤምባሲው ማስጠንቀቂያውን እንዲቀይር አሳስበዋል። ቱሪዝም ለኬንያ ከዋነኛው የውጭ ምንዛሪ ከሚያስገኙት ዘርፎች መካከል አንዱ ነው።
አርያም ተክሌ
ተክሌ የኋላ