የአሸባብ ጥቃት እና ተመድ
ሐሙስ፣ ሰኔ 13 2005
የሶማሊያ አክራሪ ደፈጣ ተዋጊ ቡድን አሸባብ ትናንት ርዕሠ-ከተማ ሞቃዲሾ በሚገኘዉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ቅጥር ግቢ ዉስጥ ባደረሰዉ ጥቃት የተገደሉት ሰዎች ቁጥር አስራ-አምስት ደርሷል።በጥቃቱ ከተገደሉት ሰወስቱ የደቡብ አፍሪቃ፥ አንዷ የኬንያ ዜጎች ሲሆኑ፥ አራቱ ቅጥር ግቢዉን ይጠብቁ የነበሩ የሶሚያሊያ ወታደሮች ናቸዉ።የተቀሩት ሰባቱ አደጋዉን የጣሉት የአሸባብ ታጣቂዎች ናቸዉ።የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ፓን ጊሙንን እና የሶማሊያ ባለሥልጣናት ጥቃቱን አዉግዘዉታል።ዓለም አቀፉ ድርጅት በጥቃቱ ሠበብ ሠራተኞቹ ከሶማሊያ እንደማያስወጣትም አስታዉቋል።ነጋሽ መሐመድ አጭር ዘገባ አለዉ።
ርዕሠ-ከተማ ሞቃዲሾ ዉስጥ በጥብቅ የማይጠበቅ የመንግሥት፥ ወይም የዉጪ ሐገራትና ድርጅቶች ተቋም የለም።ቪላ-ሞቃዲሾ፥ የሞቃዲሾ አዉሮፕላን ማረፊያ፥ የአፍሪቃ ሕብረት ጦር ሠፈር እና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ፅሕፈት ቤት የሚገኝበት ቅጥር ግቢን ያክል ጥብቅ ቁጥጥር፥ ከፍተኛ ጥበቃ የሚደረግለት የለም።የመጨረሻዉን፥-የዓለም አቀፉን ድርጅት ትልቅ ቅጥር ግቢ አሸ-ባብ ትናንት ደፈረዉ።
«የመጀመሪያዉ ጥቃት የተፈፀመዉ ከቅጥር ግቢዉ አጠገብ ነበር።የአጥፍቶ ጠፊ ጥቃት ነበር።ጥቃቱ በተፈፀመበት ቅፅበት የአሸባብ ታጣቂዎች ወደ ግቢዉ ገብተዉ እዚያ የነበሩ ሠራተኞችን በሙሉ አገቷቸዉ።»
በሞቃዲሾ የዶቸ ቬለ ተባባሪ ዘጋቢ መሐመድ ዑመር ሁሴይን።
የግቢዉ ጠባቂ ዘቦች እና የአሸባብ ታጣቂዎች ፍልሚያ ቀጠለ።ከታገቱት አራቱ ተገደሉ።ከአጋቾቹ ጋር ከሚዋጉት ዘቦች ደግሞ አራቱ ወደቁ። ከአንድ ሠዓት ግድም በኋላ የአፍሪቃ ሕብረት ጦር ታንኮች የግቢዉን አጥር እየደረመሱ ወደ ዉስጥ ዘለቁ።ከዘጠና ደቂቃ በሕዋላ ስድስት የአሸባብ ታጣቂዎች ተገደሉ።በድምሩ ሞቃዲሾ አስራ-አምስት አስከሬን ቆጠረች።እና የዓለም አቀፉ ድርጅት ቅፅር ግቢ ነፃ ወጣ፥ ወይም «ነፃ ወጣ» ተባለ።
ሚዚያ ሁለት ሺሕ ሰወስት አሸባብ ርዕሠ-ከተማ ሞቃዲሾን ለቅቆ ሲወጣ «ሞቃዲሾ ነፃ ወጣትች» ተብሎ ነብር።አክራሪዉ ቡድን ከፍተኛ ቁጥጥር የሚደረግባቸዉን የርዕሠ-ከተማይቱን አካባቢዎች ሳይቀር እስከ ዛሬ ድረስ ማጥቃቱ ነዉ-ግራ አጋቢ፥ አነጋገሪዉም ምር።
«እርግጥ ነዉ አሸባብ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ቅጥር ግቢን ብቻ ሳይሆን ርዕሠ-ከተማይቱ ዉስጥ ከፍተኛ ጥበቃ የሚደረግላቸዉን በርካታ ተቋማትና አካባቢዎችን አጥቅቷል።ባለፈዉ ወር እንኳ የሞቃዲሾን ከፍተኛ ፍርድ ቤት አጥቅቷል።የአሸባብ ተዋጊዎች ከማጥቃታቸዉ በፊት የሚያጠቁትን አካባቢ፥ የሚያጠቁበትን ጊዜና ሥልት በጥንቃቄ ያጠናሉ።ያሁኑ ጥቃትም እንደዚያ ነዉ።መጨረሻ ላይ ፈፀሙት»
ይላል ጋዜጠኛዉ።
ሹ
ፕሬዝዳት ሐሰን ሼኽ መሐሙድ የሚመሩት መንግሥት ከተመሠረተ በተለይ ደግሞ ዩጋንዳ መራሹ የአፍሪቃ ሕብረት ጦር ሥልታዊቱን የወደብ ከተማ ኪስማዩን ከአሸባብ እጅ አስለቅቆ ከተቆጣጠረ ወዲሕ አክራሪዉ ደፈጣ ተዋጊ ቡድን ክፉኛ መዳከሙ በሰፊዉ ሲነገር ነበር።በሶማሊያ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ልዩ መልዕክተኛ ኒኮላስ ኬይ ከትናንቱ ጥቃት በኋላ እንዳሉት ግን አሸባብ አሁንም በጋራ ሊዋጉት የሚገባ ጠንካራ ቡድን ነዉ።
«አሸባብ ከሶማሊያ ከተሞች መባበረሩ እዉነት ነዉ።ይሁንና ሁላችንም እንደምናዉቀዉ አሸባብ አሁንም እየተንቀሳቀሰ ነዉ።በሶማሊያ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ተወካይ ኬይም ከትናንቱ ጥቃት በኋላ ይሕንን አምነዋል። «አሸባብ አሁንም በንቃት የሚንቀሳቀስ ቡድን ሥለሆነ በጋራ ልንዋጋዉ ይገባል ብለዋል።»
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በትናንቱ ጥቃት ምክንያት ሠራተኞቹን ከሞቃዲሾ እንደማያስወጣ አስታዉቋል።ይሁንና የሶማሊያ መንግሥት ለድርጅቱ ሠራተኞች ተጨማሪ ጥበቃ እንዲያደርግ ዋና ፀሐፊ ፓን ጊ ሙን ጠይቀዋል።
ነጋሽ መሐመድ
አርያም ተክሌ