የአረንጓዴ ጀግና
ማክሰኞ፣ ሰኔ 25 2005ከባህር ማዶ ወደአገር ቤት ከሚመለሱ ብዙሃኑ ወደተለያዩ የንግድ ዘርፎች መሰማራትን እንደሚያዘወትሩ ይስተዋላል። የእሳቸዉ ሙከራ ግን ሌላ ነዉ። የተራቆተዉን አካባቢ በአገር በቀል ዛፎች መልሶ እንዲያሸበርቅ ማስቻል።
ከስምንት ሺህ በላይ ልዩ ልዩ አገር በቀል እጽዋትን ተክለዋል። ባህር ዳር በአባይ ወንዝ ዳርቻ። በዚህ ተግባር ከተሰማሩ ከአስር ዓመት በላይ ሆኗል። የተከሏቸዉ ታዲያ እንደዉ ችግኝ ተተከለ ለማለት ብቻ ሳይሆን ለፍሬ በቅተዋል። አቶ አሰፋ ታዬ የሚበሉ ፍራፍሬዎች፤ ለመድሃኒት የሚሆኑ ተክሎች፤ እንዲሁም ሌሎች አትክልቶችን በመትከል ለኅብረተሰቡ እንደሚያቀርቡ፤ ችግኞችን እያፈሉም ለተጠቃሚዎች እንደሚያዳርሱ አጫዉተዉናል። ለዚህ ተግባር ያነሳሳቸዉ ደግሞ አካባቢዉ ተራቁቶ እና ተጎሳቁሎ ማየታቸዉ ነዉ።
አቶ አሰፋ ሁለት ሄክታር መሬት ላይ ነዉ ይህን ተግባር የሚያከናዉኑት። ሃያ ስድስት ዓመታትን ካሳለፉባት አሜሪካ ወደአገራቸዉ በግብርናዉ ዘርፍ የመሰማራት ምኞት ይዘዉ ነበር ከ14ዓመታት በፊት የተመለሱት።
ከአካባቢዉ አስተዳደር፤ ከቀበሌዎችና ከኅብረተሰቡ ማበራታቻ ማግኘታቸዉን የሚገልፁት አቶ አሰፋ በግላቸዉ የተራቆተዉን አካባቢ እጽዋት ለማልበስ ጥረታቸዉን ቀጠሉ። በዚህ ብቻ ግን አላቆሙም አቶ አሰፋ አሜሪካ የኖሩባት ከተማ ኦክላንድ ከባህር ዳር ጋ እህትማማች ከተማ እንድትሆን አስተባብረዋል፤ ለአርሶ አደሩ የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲዳረስም ከፀሐይ ኃይል መብራት የሚገኝበትን ስልት እያቀረቡ እንደሆነም ገልፀዉልናል። ከዚህም ሌላ ከበጎ አድራጎት ድርጅቶች ጋ በበጎ ፈቃደኝነት የበኩላቸዉንም ያደርጋሉ። ለአካባቢ ጥበቃ ባደረጉት አስተዋጽኦም ዘንድሮ ተሸላሚ ሆነዋል። ሌሎችም የእሳቸዉን አርአያ እንዲከተሉም ይመኛሉ።
ሸዋዬ ለገሠ
ሂሩት መለሰ