የአሜሪካን ፊልምና የሙስሊሞች ተቃውሞ
ዓርብ፣ መስከረም 4 2005ካይሮ ውስጥ፤ ነቢዩ መሀመድን የሚጎንጥ ፊልም መሠራቱንና ለእይታ መቅረቡን በመቃወም ዛሬ አሜሪካ ኤምባሲ በር ከፖሊስ ጋር መጋጨታቸው ተነገረ። መሀመድ ሙርሲን ለፕሬዚዳንትነት ያበቃው የግብፁ የሙስሊም ወንድማማች ማኅበር የተሰኘው ፓርቲም አገር አቀፍ የተቃውሞ ሰልፍ እንዲደረግ ጥሪ ማስተላለፉ ተነግሯል። የመን ውስጥ ትናንት የአሜሪካ ኤምባሲ ሲወረርአንድ ሰው መገደሉና 15 መቁሰላቸው ታውቋል። በካሊፎርኒያ ዩናይትድ እስቴትስ የተሠራውንና የነቢዩ መሐመድን ክብር የሚነካ መሆኑ የተነገረለትን ፊልም በመቃወም በማሌሺያ፤ ባንግላዴሽ እና ኢራቅ ሙስሊሞች አደባባይ ወጥተዋል። በካርቱም ፤ የሱዳን መንግሥት ያበረታታቸው ሙስሊም ምሁራንና በአጠቃላይ 5,000 ያህል የተቃውሞ ሰልፈኞች ፤ ከዕለተ ዓርብ ጸሎትና ስግደት በኋላ አደባባይ በመውጣት ፤ የጀርመንና የብሪታንያን ኤምባሲዎች ሲወሩ ፣ የሱዳን ፖሊስ የሚያስለቅስ ጋዝ በመርጨት የገታቸው መሆኑ ተመልክቷል። ጎን ለጎን የሚገኙት የሁለቱ አገሮች ኤምባሲዎች በድንጋይ ውርወራ መጠቃታቸው ተነግሯል። በናይጀሪያ ፣ መንግሥት፣ ለውጭ ሃገራት ኤምባሲዎች ጥበቃ ፣ ፀጥታ አስከባሪዎች በተጠንቀቅ ላይ እንዲገኙ ማድረጉ ታውቋል።
ጀርመን፤ በዐረቡ ዓለም በሚገኙ ኤምባሲዎቿ ጥበቃው እንዲጠናከር ያደረገች ሲሆን፤ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ጊዶ ቬስተርቨለ፣
የሌሎችን የሃይማኖት ስሜት ለመጎንተል በተሠራው አማተር ቪዲዮ ፊልም ላይ የቀረበውን ውግዘትና ነቀፌታ እንጋራለን፤ ነገር ግን ይህ በምንም ዓይነት ለሁከትና ግድያ ምክንያት ሊሆን አይችልም ማለታቸው ተጠቅሷል። ቬስተርቨለ በሱዳን የተፈጠረውን ሁኔታ በተመለከተ የሚከተለውን መግለጫ ሰጥተዋል።
«በተለያዩ አገሮች ስለሚያጋጥም ሁኔታ አዘውትረን ዘገባ እናቀርባለን። ከዚህም ጋር ይፋ በሚቀርቡ የውጭ ጉዳይ ሚንስቴሩ የመረጃ ምንጮች መሠረት መመሪያ ይሰጣል ። ዋናው ጠቀሚ ጉዳይ እንደኛ እምነት፤ ጥንቁቅ መሆን፤ እርስ-በርስ መተሳሰብ፤ አደጋ ባጋጠማቸው ቦታዎች ፤ በቁጣ ገንፍለው ከተሰበሰቡ ሰዎች አጠገብ አለመቅረብ ነው። የሆነው ሆኖ፤ እስከዚህ ሰዓት ድረስ፤ አጠቃላይ የሆነ ወደ እስላማውያን አገሮች የሚደረግ ጉዞን በተመለከተ ለውጥ የሚደረግበት መመሪያ አላቀረብንም።»
ይህ በእንዲህ እንዳለ የፊልሙ ሠሪ ነኝ ያሉት ፣ በካሊፎርኒያ የሚኖሩ ፣ ናኩላ ባሲሊ ናኩላ የተባሉ የ 55 ዓመት ጎልማሳ ቅብጣዊ ክርስቲያን፤ ፊልሙን በመሥራቴ አልጸጸትም ሲሉ በራዲዮ መግለጻቸው ታውቋል። ክብር ነክ የተባለውን ፊልም በመሥራቱ ረገድ፣ አንዳንድ አሜሪካውያን አክራሪ ወንጌላውያን ክርስቲያኖችም ሳይኖሩበት እንዳልቀረ ተመልክቷል።
ተክሌ የኋላ
ሂሩት መለሰ