የአልዛይመር በሽታ
ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 13 2007ጀርመን ውስጥ ከ 1,5 ሚሊዮን ሰዎች በላይ የአልዛይመር በሽታ ተጎጂ ናቸው። የአንጎል የነርቭ ሴሎች ሲሞቱ ሰዎች መርሳት ይጀምራሉ፤ የመናገር እና የማስታወስ ችሎታቸውም ይዳከማል። እንደ የጀርመን የአልዛይመር ማህበረሰብ መረጃ የታማሚው ቁጥር እስከ 2050 ዓም በእጥፍ ሊጨምር ይችላል። አብዛኛውን ጊዜ ሰዎች ስለበሽታው በቂ ግንዛቤም ስለሌላቸው አንድ ሰው በበሽታው መያዙ የሚረጋገጠው ጉዳቱ ስር ከሰደደ በኋላ ነው።
እስካሁን የተደረጉ የህክምና ጥናቶች እንደሚያሳዩት፤ በሽታውን ማዳን አይቻልም። ይህ በሽታ ለመሆኑ ምንድን ነው? በዩናይትድ ስቴትስ የነርቭ እና የስነ- አዕምሮ ባለሙያ ፕሮፌሰር ዮናስ እንዳለ ገዳ የዶይቸ ቬለ ገልፀዋል። እስካሁን ያለው ተሞክሮ እንደሚያሳየው፤ አብዛኞቹ የአልዛይመር ታማሚዎች ከ 80 ዓመት በላይ የሆኑ አዛውንቶች ሲሆኑ፤ 70 ከመቶ የሚሆኑት ደግሞ ሴቶች ናቸው። ይሁንና በሽታው በጎልማሳ እድሜም ሊይዝ ይችላል።
የህክምና ባለሙያዎች እና ተመራማሪዎች የአልዛይመር መንስኤን ባያቁም ፤በሽታው አንድ ሰው ላይ ቀድሞ ሲስተዋል ፤ ሙሉ በሙሉ ማዳን ባይቻልም እንዳይባባስ ማድረግ ይቻላል የሚለውን ሀሳብ ይጋራሉ። የነርቭ ችግር ያለባቸው ሰዎች በቂ ክትትል እና ልዩ ስልጠና ያገኘ ሰው እንደሚያስፈልጋቸውም ሐኪሞች ይመክራሉ።
በአለም ዙሪያ 44 ሚሊዮን የሚደርሱ ሰዎች የአልዛይመር በሽታ ተጠቂ እንደሆኑ ይገመታል። የአንድ ሰው የመኖር አማካይ እድሜም ከፍ እያለ ስለሚሄድ በአለም ዙሪያ እኢአ እስከ 2050 ዓ ም ድረስ የታማሚው ቁጥር 135 ሚሊዮን ሊደርስ እንደሚችል ይገመታል። በሽታው ምን ያህል እድሜ ይሰጣል? በሽታውንስ እንዴት መከላከል ይቻላል? ለዚህ እና የሌሎች ጥያቄዎች ፕሮፌሰር ዮናስ እንዳለ ገዳ መልስ ሰጥተውናል።
ከድምፅ ዘገባው ያገኙታል።
ልደት አበበ
ሂሩት መለሰ