የትንኝ ስጋት በደቡብ ወሎ
ማክሰኞ፣ ኅዳር 6 2009እነሱ እንደሚሉት በደቡብ ወሎ አምባሰል በሚገኙ አካባቢዎች በብዛት ትንኝ ወይም ጢንዚዛ ያሏት በራሪ ፍጥረት በበርካታ ሰዎች ጆሮ ዉስጥ ገብታ ሰዎቹ ተቸግረዋል። በዘመናዊ ህክምና እርዳታ ማግኘት ስለማይችሉም ለማስወጣት ባህላዊ መድኃኒት አድራጊዎች ጋር መሄድ ይኖርባቸዋል። ስለሚባለዉ ነገር ሰምተናል ከሚሉ አንስቶ፤ ሊወጣላቸዉ ወደ ባህል ህክምና አዋቂዎች ዘንድ የመጡትን አይተናል አነጋግረናል የሚሉም አሉ። በተቃራኒዉ የጆሮ ህክምና ባለሙያ የሆኑ አንድ ሀኪም ደግሞ ጉዳዩ የስነልቡና ችግር እንደሆነ ይህን የሚሉትን ችግር ማለትም ስለአንድ ጉዳይ እያሰቡ ያ እንደሆነ አድርጎ ማመን እና ያንንም ብዙዎች አምነዉ የዚያ ሃሳብ ተጋሪ እንዲሆኑ የሚያበቃ መዘዝ እንዳይከተል ለጤና ቢሮዉ ጠቁሜ ነበርም ይላሉ። የደቡብ ወሎ ዞን ጤና መምሪያ ቢሮ ጉዳዩን ከኅብረተሰቡ መስማቱን፤ እንዲያጣራም ሀኪሞች የተካተቱበት ቡድን ማሰማራቱን ይናገራል። ከሚወራዉ ያለፈ ግን በተጨባጭ በባህል ህክምናዉ ወጥቶ የታየ ትንኝም ሆነ ጢንዚዛ የለም ነዉ የሚለዉ የጤና ቢሮዉ። መንስኤዉ እየተጣራ ሲሆን ለኅብረተሰቡ ሊሰጥ የሚችለዉ የዘመናዊ ህክምና ምን ሊሆን እንደሚችልም አብሮ እየተመረመረ መሆኑንም አስረድቷል። ዋናዉ ነገር እስካሁን በዚህ ችግር የሰዉ ህይወት አላለፈም። ይህም እማኝነን በሚሉትም ሆነ በጤና ቢሮዉ ባለስልጣን ተገልጿል። ዝርዝሩን ከድምጽ ዘገባዉ ይከታተሉ።
ሸዋዬ ለገሠ
ነጋሽ መሐመድ