የትርምፕ መርሕ፤ ዉይይት
እሑድ፣ ጥር 28 2009
የዛሬዉ ዉይይታችን የዩናይትድ ስቴንስ አዲስ ፕሬዝደንት መርሕ ወይም ፖሊሲ በዓለም ላይ በሚያሳድረዉ ተፅዕኖ ላይ ያተኩራል። ሰዉዬዉ በብዙ ነገር ከቀዳሚ የሐገራቸዉ መሪዎች ይለያሉ።እርግጥ ነዉ ጆን ኤፍ ኬኔዴ ሐብት ሞልቶ የተረፈዉ ቤተ-ሰብ ልጅ ነበሩ።የቢሊዮነ-ቢሊዮናት ዶላር ጌታ ሆነዉ ዋይት ሐዉስ የገቡ የመጀመሪያዉ መሪ ናቸዉ።
የቀድሞዉ የፊልም ተዋኝ ሮናልድ ሬጋን እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር በ1980 ፕሬዝደንት ሲሆኑ የመጀመሪያዉ ሽማግሌ ፕሬዝደንት ተብለዉ ነበር።ዘንድሮ ትራምፕ በለጧቸዉ።ሰባ ዓመታቸዉ።ምንም አይነት የፖለቲካ ልምድ ሳይኖራቸዉ የትልቂቱን ሐገር ትልቅ የፖለቲካ ሥልጣን በመያዝም የመጀመሪያዉ ናቸዉ።
ሁለተኛ ሚስታቸዉን ይዘዉ ዋይትሐዉስ የገቡ የመጀመሪያዉ መሪ አሁንም ሬጋን ነበሩ።ሰወስተኛ ሚስታቸዉ ቀዳሚዊት እመቤት በማሰኘት ግን እሳቸዉ የመጀመሪያዉ ሆኑ።ዶናልድ ጆን ትራምፕ።ጉዳያችን በርግጥ መርሕ ወይም ፖሊሲያቸዉ ናቸዉ።በዚሕም የቀደማቸዉ የለም።ባጭር ጊዜ ዉስጥ በርካታ ፕሬዝደንታዊ አዋጆች፤ ደንቦች ወይም መመሪያዎች በማፅደቅ የመጀመሪያዉ ናቸዉ።ሥልጣን በያዙ በአስር ቀናት ዉስጥ ሰባት ፕሬዝደንታዊ ትዕዛዞች፤ አስራ-አንድ አዋጆች ወይም ደንቦች አፅድቅዋል። በአዋጅ፤ ደንብ፤ ወይም ትዕዛዞቻቸዉ የንግድ ስምምነቶችን ሰርዘዋል፤ ድንበር እንዲታጠር ወስነዋል፤ ሰዎችን ላለማፈናቀል ወይም የተፈጥሮ ሐብትን ለማስጠበቅ የታገደ የነዳጅ መስመር ዝርጋታን ፈቅደዋል።የበርሊን ግንብ መፍረሱ የሕዝብን ፍላጎት የመጠበቅ፤ የሰዉን የመንቀሳቀስ ሰብአዊ መብት የማስከበር ፍትሐዊ እርምጃ መሆኑ በእንደ አብነት በሚደነቅ፤ በሚነገር፤ በሚፃፍበት ዘመን አሁን፤ ሰዉዬዉ ከ3ሺሕ ኪሎ ሜትር በላይ የሚረዝመዉን የትልቂቱን ሐገር ድንበር በግንብ እንዲታጠር አዘዋል።ትዕዛዙ አልበቃ ያለ-ይመሰል አሜሪካን ለማጠር የሚያስፈልገዉን ወጪ ሚክሲኮ ለማስከፈል መዛታቸዉ ብዙዎችን ሲያስገርም፤ ሜክሲኮዎችን አስደንግጧል።አብዛኞቹ ደንብ-አዋጆቻቸዉ አወዛጋቢ ናቸዉ። ውይይቱን የድምፅ ማዳመጫውን ተጭነው ያዳምጡ።
ነጋሽ መሐመድ
ልደት አበበ