የትራምፕ ቀዉስ
ሐሙስ፣ ሰኔ 1 2009የዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ በምርጫ ዘመቻቸዉ ወቅት ከሩሲያ ድጋፍ አግኝተዋል የሚለዉ ጥርጣሬ እንዳይጣራ ከፍተኛ ግፊት ማድረጋቸዉን የሚጠቁም መረጃ እንዳገኙ የሐገሪቱ ሴናተሮች አጋለጡ።ትራምፕ ከሥልጣን ያበረሯቸዉ የቀድሞዉ የምርመራ ቢሮ (FBI) ኃላፊ የጄምስ ኮሜይን ምስክርነት ያደመጠዉ የሐገሪቱ ሕግ-መወሰኛ ምክር ቤት የስለላ ኮሚቴ አባላት እንደሚሉት የሩሲያ ጣልቃ ገብነት እንዳይጣራ ትራምፕ ኮሜይን ከሥራ እስከ ማባረር ድረስ ዝተዉ ነበር።ዝተዉ አልቀሩም ኮሜይን አባረሩ።ዴሞክራቱ ሴናተር ሮን ዉይደን የኮሚን ማብራሪያ እንደ ጥሩ ልብ ወለድ የሚፈስ ብለዉታል።
«የኮሜይ መግለጫ ለምክር ቤት ከሚቀርብ ማብራሪያና ምሥክርነት ይልቅ እንደ ቶም ክላንሲ ልብ ወለድ መፅሐፍ የሚፈስ ነዉ።ኮሜይ ለፕሬዝደንቱ ታማኝ እንዲሆኑ ከፍተኛ ግፊት ያደርጉባቸዉ እንደነበር ገልፀዋል።በፍሌይን (የቀድሞዉ የትራምፕ አማካሪ) ላይ የሚደረገዉ ምርመራም እንዲድበሰበስ ፕሬዝደንቱ ሞክረዋል።ይሕ ብቻ የዎተርጌቱ ቅሌት እንዳይጣራ ተደርጎ ከነበረዉ ጣልቃ ገብነት ጋር የሚመሳሰል ነዉ።»
ሪፐብሊካን የኮሚቴዉ አባላት ግን ፕሬዝደንት ትራምፕ እንደማንኛዉም ፕሬዝደንት የሹሞቻቸዉን ታማኝነት ለማግኘት ከመጣር ባለፈ ያደረጉት የለም ባይ ናቸዉ።ሌለኛዉ የዴሞክራቲክ ፓርቲ የኮሚቴዉ አባል ሴናተር ማርክ ዎርነር ግን ከኮሜይ የሰሙትን «የሚረብሽ» ብለዉታል።
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሰ