የታሰሩት የፓርላማ አባላት ጉዳይ እና ረሃብ አድማ የመቱ እስረኞች ጉዳይ
ሰኞ፣ ነሐሴ 15 2015በቅርቡ በቁጥጥር ሥር የዋሉት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል አቶ ክርስትያን ታደለ እና የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባል የሆኑት ግለሰብ ዛሬ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎ የነበረ ቢሆንም ሳይቀርቡ መቅረታቸውን ጠበቃቸው ገለፁ።
ከጠበቆቻቸው አንዱ ጠበቃ ሰለሞን ገዛኻኝ ታሳሪዎቹ ፍርድ ቤት እንደሚቀርቡ ሰምተው የነበረው ከቤተሰቦቻቸው መሆኑን ገልፀዋል። በሌላ በኩል በፌደራል ዐቃቤ ሕግ በሽብር ወንጀል ክስ ቀርቦባቸው ጉዳያቸው ለጥቅምት 15 ቀን 2016 ዓ.ም ቀጠሮ የተሰጠበት 51 ተከሳሾች በማረሚያ ቤት ውስጥ እያሉ የሦስት ቀናት የረሀብ አድማ ማድረጋቸው ተገለፀ።
ታራሚዎቹ የረሃብ አድማ ያደረጉት መንግሥት በአማራ ተወላጆች ላይ እየፈፀመ ነው ያሉትን ነፃ እርምጃ እና ግድያ በአስቸኳይ እንዲያቆም እንዲሁም በአዲስ አበባ ከተማ እና በሌሎች አካባቢዎች እየተፈፀመ ነው ያሉት የጅምላ እሥር እንዲቆም የጠየቁበት መሆኑን ለማወቅ ተችሏላ።
በአማራ ክልል ጦርነት ከተከሰተ በኋላ የታወጀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተከትሎ ከሳምንታት በፊት ከመኖሪያ ቤታቸው በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተያዙት
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባሉ አቶ ክርስትያን ታደለ እና የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት አባል የሆኑት ዶክተር ካሳ ተሻገር ዛሬ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ የሚል መረጃ ከቤተሰቦቻቸው ደርሷቸው እንደነበር የገለፁት ጠበቃ ሰለሞን ገዛኸኝ ከማለዳው ጀምሮ በልደታ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቢገኙም ደንበኞቻቸው ፍርድ ቤት አለመቅረባቸውን ገልፀዋል።
በሌላ በኩል በፌደራል ዐቃቤ ሕግ በሽብር ወንጀል ክስ ቀርቦባቸው ጉዳያቸው ለጥቅምት 15 ቀን 2016 ዓ.ም ቀጠሮ የተሰጠበት 51 ተከሳሾች በማረሚያ ቤት ውስጥ እያሉ ከአርብ ጀምሮ የሦስት ቀናት የረሀብ አድማ ማድረጋቸው ተገለፀ።
ታራሚዎቹ ይህንኑ አስምልክቶ በቤተሰቦቻቸው በኩል ባወጡት ጽሁፍ መንግሥት "የአማራ ተወላጆች ላይ እየፈፀመ ያለው ነፃ እርምጃ እና ግድያ በአስቸኳይ እንዲቆም" ይጠይቃል።
በአዲስ አበባ ከተማና በአንዳንድ ከክልሉ ውጭ ባሉ አካባቢዎች የአማራ ተወላጆች መታሰራቸው እንዲቆምና እንዲፈቱ የሚለው ሌላኛው የረሃብ አድማው ምክንያት መሆኑንም ጠቅሰዋል።
ሰሎሞን ሙጬ
አዜብ ታደሰ
ማንተጋፍቶት ስለሺ