የታሠሩት የሙስሊም ተወካዮች ፍርድና የሌሎች መታሰር
ሐሙስ፣ ጥቅምት 15 2005
የኢትዮጵያ ፖሊስ በአሸባሪነት ጥርጣሬ ያሠራቸዉን የሙስሊሞች የእርቅና የመፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላትና ተባባሪዎቻቸዉን እንዲፈታ ጠበቆቻቸዉ ጠየቁ።ለስምንት የኮሚቴዉ አባላትና ለአስራ-ስድስት ተባባሪዎቻቸዉ ጥብቅና ከቆሙት አንዱ አቶ ተማም አባ ቡልጎ እንዳስታወቁት ፖሊስ ምርመራዉን አጠናቆ በተጠርጣሪዎቹ ላይ ክስ እንዲመሰርት ፍርድ ቤት ለትናንት የመጨረሻ ቀጠሮ ሰጥቶ ነበር።ፖሊስ ግን ተጠርጣሪዎቹንም ሆነ ክሱን ፍርድ ቤት አላቀረበም፥ ምክንያቱንም አላስታወቀም።ፖሊስ ቀጠሮዉን ባለማክበሩ ምክንያት ፍርድ ቤቱ መዝገቡን ዘግቶቷል።በዚሕም ምክያት ጠበቃ ተመማም እንደሚሉት ደንበኞቻቸዉ ከትናንት ማታ ጀምሮ መታሰራቸዉ ሕገ-ወጥ ነዉ።ነጋሽ መሐመድ አቶ ተማም አባ ቡልጎን በሥልክ አነጋግሯቸዋል።----በሌላ በኩልደቡብ ወሎ ገርባ በተባለችዉ ከተማ ባለፈዉ እሁድ የሐይማኖት ነፃነታችን ይከበር በሚሉ ሙስሊም የአካባቢዉ ነዋሪዎችና በፀጥታ አስከባሪዎች መካካል በተነሳ ግጭት ሰዎች ከተገደሉ ወዲሕ በርካታ ሰዎች መታሰራቸዉን የአካባቢዉ ነዋሪዎች አስታወቁ።የገርባ፥ የደጋን፥ የሐርቡ ነዋሪዎች እንዳስታወቁት ፖሊስ ከየከተማዉ ሰዎችን እየያዘ ወደ ኮምቦልቻ እየወሰደ አስሯል።ኮምቦልቻ ወሕኒ ቤት ከታሰሩት የተወሰኑትን ዛሬ አነጋግሬያለሁ ያሉ አንድ የአይን ምስክር እንደገለፁት ከእስረኞቹ መካካል እድሜያቸዉ ሰባና ሰማንያ ዓመት የሚደርስ አዛዉታት ይገኙባቸዋል።ነጋሽ መሐመድ የዓይን ምስክሩን በስልክ አነጋግሯቸዋል።
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሠ