የተመኙት የስራ መስክና ፈተናው
ዓርብ፣ ነሐሴ 30 2006ወደሚፈልጉት የሙያ ዘርፍ ለመግባት የተለያዩ ነገሮች ቁልፍ ሚና ይጫወታሉ። ተሰጥስዎ፣ የትምህርት እድል፣ ፍላጎት የመሣሰሉት ጥቂቶቹ ናቸው። አንዳንዶች የበፊቱ ምኞታቸው አሁን ካለው ጋር ፍፁም ተቃራኒ ሆኖ ሲያገኙ ሌሎች ደግሞ በዚሁ የሙያ መስክ ገፍተው የስራውን ዓለም ይቀላቀላሉ።
የ24 አመቷ መክሊት መርሻ ከሁለት ዓመት በፊት በማህበራዊ ሳይንስ ወይም ሶሲዮሎጂ በከፍተኛ ደረጃ ትምህርት አጠናቃለች።ዛሬ ግን በተማረችበት ሙያ አትሰራም። እሷ እንደምትለው ከመጀመሪያ ጀምሮ ፍላጎቷ ሌላ ነበር። መክሊት መለስ ብላ ስለምኞቷ ስታስታውስ ፎቶ ማንሳት ያስደስታታል። መክሊት ዛሬ ለሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር መፅሄቶች ለማስተዋወቂያ የሚሆኑ ፎቶዎች እያነሳች ትሸጣለች። ወጣቷ መሆን የምትፈልገውን ወይንም አቅጣጫዋን አስቀድማ ብታውቅም በወቅቱ በምርጫዋ ብዙዎች እንደማይረኩ ታውቅ ነበር። ለዚህም ነው ስለ የማህበራዊ ኑሮ ለማጥናት የወሰንኩት ትላለች።
ሌላው ያነጋገርነው በንቲ እጄታን ነው። በንቲ ከመጀመሪያ ጀምሮ የሚፈልገውን የትምህርት ዓይነት ነው የተከታተለው። ጋዜጠኝነት። ለተወሰኑ ዓመታት ለቴሌቪዥን እና ሬዲዮ ሰርቷል። ይሁንና በንቲ ዛሬ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን እና ሬዲዮ ድርጅት እየሰራ አይደለም፤ መስሪያ ቤት ቀይሯል። ስለ አዲሱ ስራው እና ወደፊት ሊሰራው ስለሚፈልገው ያብራራል።
ምስራቅ ተረፈ ከልጅነቷ ጀምሮ የምትፈልገውን የሙያ ዘርፍ አልቀየረችም። በዚህም ፍላጎት ላይ ተመርኩዟ ይህንን ዕውን ለማድረግ እየሰራች ትገኛለች። ምስራቅ ዛሬ መድረኮች ላይ ቀርባ ግጥሞቿን ታነባለች። ከዚህም ሌላ ግጥሞቿ ታትመው ወጥተዋል። እንዲሁም በምስል እና በድምፅ የታቀፈ ቪዲዮ ለማውጣት ችላለች። «እነዚህ ነገሮች ምርጫዬ ትክክል እንደነበርና ፤ ነኝ ያልኩትን ለመሆኔ ማሳያ ሆነውኛል ትላለች ምስራቅ፤ እዚህ እስክትደርስ የነበረውን ውጣ ውረድ እያስታወሰች።
ወጣቶች በተመኙት የስራ መስክ ለመሰማራት ስለሚያደርጉት ትግል በዛሬው የወጣቶች ዓለም የቃኘነው ርዕስ ነው። ሙሉ ዘገባውን ከዚህ በታች በድምፅ ያገኙታል።
ልደት አበበ
አርያም ተክሌ