የባህል መድረክ
ሐሙስ፣ ጥር 23 2005በተመ የትምሕርት፥የሳይንስና የባሕል ድርጅት በእንግሊዘኛ በምህፃሩ(UNESCO)ጥበቃ ስር በዓለም ቅርስነት የተመዘገበችዉ ጥንታዊትዋ የሰሜን ማሊ ከተማ ቱምቢክቱ ለበርካታ ወራት በጽንፈኛ እስላማዊ ቡድኖች በተያዘች ግዜ በርካታ ጥንታዊ ታሪክን የያዙ መጻህፍት፤ ተቃጥለዋል፤ ጥንታዊ የባህል መገላጫ የሆኑ ህንጻዎችም በዓማጽያኑ ወድመዋል ተብሎአል። በያዝነዉ ሳምንት ረዕቡ በፈረንሳይ ወታደሮች የሚታገዙት የማሊ መንግስት ወታደሮች ከተማይቱን መልሰዉ በጃቸዉ ማስገባታቸዉ ከተነገረ ከአንድ ቀን በኋላ በደቡብ አፍሪቃ የሚገኘዉ ዩንቨርስቲ ባወጣዉ ዘገባዉ በሰሜናዊ ማሊ ቲብቡክቱ በቅርስነት ተይዘዉ የነበሩት ጥንታዊ ጽሁፎች እጅግ ጥቂቱ ብቻ ጠፍተዋል አልያም ተቃጥለዋል ሲል ዘገባዉን ይፋ አድርጎአል። አክራሪ ሙስሊሞቹ የሸርያ ህግን ተፈጻሚ እንዲሆን ሲጠይቁ የአፍሪቃ ባህላዊ ሙዚቃ እንብርት መሆንዋ በሚነገርባት በማሊም ሙዚቃ እንዳይደመጥ እና እንዳይዜም በጽኑ ከልክለዋል። "Festival in the Desert", የበረሃዉ ፊስቲቫል በመባል የሚታወቀዉ በሰሜናዊ ማሊ ቲምቡክቱ ከተማ ከአስር ዓመት በላይ በመካሄድ ላይ ያለዉ የሙዚቃ ድግስ፤ ታዋቂ የዓለም ሙዚቀኞችን ቀልብ ስቦ በርካታ ሙዚቀኞችን ከዓለም ዙርያ በማሰባሰቡ ይታወቃል። የቲምቡክቱ የሙዚቃ ድግስ ማለት « በረሃዉ ፊስቲቫል» ቲምቡክቱ በፅንፈኞቹ እጅ ስር ከወደቀች በኋላ ሙዚቃ በመከልከሉ ታግዶአል። የማሊ ሙዚቀኞች በበኩላቸዉ፤ የባህል መገለጫችን የሆነዉን ሙዚቃችን ዳግም ለመድረክ ለማብቃት እንታገላለን የዓለም ሙዚቀኞችም የመድረካችን ተካፋዮች እንዲሆኑ ጥረታችንን እንቀጥላለን ማለታቸዉ ተነግሮአል።
ኮራ በምዕራብ አፍሪቃ ሀገራት የሚገኝ ባህላዊ የሙዚቃ መሳርያ ነዉ። በዋና መዲና ባማኮ የሚገኘዉዉ አነስተኛ ግን ታዋቂዉ ፒሊፒሊ ቡና ቤት ለደንበኞቹ የሚያቀርበዉ፤ ጣዕም ያለዉ ምግብ ብቻ ሳይሆን የባህላዊ የሙዚቃ መሳርያን የሚጫወቱ በርካታ ታዋቂ ሙዚቀኞችን ወደ መድረክ በመጋበዙም ነዉ። ኮራን የተሰኘዉን ባህላዊ የሙዚቃ መሳርያ ድንቅ አድርጎ በመጫወቱ በዓለም ዝናን ያተረፈዉ የማሊ ተወላጅ ያኩባ ሲሶኮ በማሊ መዲና ባማኮ ፒሊ ፒሊ ቡና ቤት መድረክ ላይ ይጫወታል ።ያኩባ ሲሶኮ ወደ ቡና ቤቱ ሲገባ ሙዚቃዉን ለማዳመጥ የሚገቡት የቡና ቤቱ ታዳሚዎች ቁጥር እጅግ ይጨምራል ። ለማሊ ተወላጆች ሙዚቃ የህይወት ነዉ፤ የእየ እለት የህይወት ገጠመኞቻቸዉን የሚተርኩት በሙዚቃ ነዉ። በሰሜናዊ ማሊ አክራሪ እስላማዉያኑ አካባቢዉን ከተቆጣጠሩ ጀምሮ ግን ህዝቡ ሙዚቃን እንዳይጫወት ታግዶ ነበር።
ሰሚናዊ ማሊ ጋዎ ነዋሪ ከነበሩ እና እስላማዊ አማጽያንን ፈርተዉ ወደ መዲና ባማኮ ከሸሹ እዉቅ ባህላዊ ሙዚቀኞች መካከል ዞዙ አንዱ ናቸዉ። በዲሞክራሲያዊ መንገድ ስልጣን ላይ የወጣዉ የማሊ መንግስት ባለፈዉ የጎርጎረሳዉያኑ ዓመት መጀመርያ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ከተደረገበት በኋላ የከአልቃይዳ ጋር ግንኙነት እንዳላቸዉ የሚነገርላቸዉ ሙስሊም አማፅያን ሰሜናዊ ማሊን ተቆጣጥረዉ ማንኛዉም ሙዚቃ እንዳይደመጥ አገዱ፤ ሙዚቃን ብቻ አይደለም ከዚህም አልፈዉ ተንቀሳቃሽ ስልክ የሚያሰማዉን የመደወያ ድምጽንም ጭምር ማገዳቸዉ ተገልጾአል። ሙዚቀኛ ዛዙ እንደሚሉት ህዝቡም ሆነ ሙዚቀኛዉ እየተሰቃየ ነዉ።
«በጣም አዝኛለሁ ጥሩ ስሜት የለኝም ምክንያቱም እኔ ራሴ ከዝያዉ ሰሜን ማሊ ነዉ የመጣሁት። ቤተሰቦቼም በስቃይ ላይ እዝያዉ ሰሜናዊ ማሊ ነዉ የሚገኙት፤ ሙዚቀኞችም ቢሆኑ በስቃይ ላይ ናቸዉ» በያዝናዉ ሳምንት መጀመርያ በፈረንሳይ ወታደሮች የሚታገዙት የማሊ ወታደሮች ሰሜናዊ ማሊን አብዛኛዉን ክፍል ከአማጽያኑ አስለቅቀዋል። በዓለም ቅርስ መዝገብ ዉስጥ የተካተተችዉን የቱምቢክቱን ባህላዊ እሴቶች ለመታደግ ብሎም ለማሊ ቀውስ ፖለቲካዊ መፍትሔ እንደሚያስፈልግም ተገልጾአል። በአፍሪቃ ህብረት መዲና አዲስ አበባ በተካሄደዉ የማሊ ዓለም አቀፍ የለጋሽ ሀገራት ጉባዔ ላይ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለማሊ 455,53 ሚልዮን የአሜሪካን ዶላር ድጋፍ ለመስጠት ቃል መግባቱ፤ በማሊ ባህላዊ የሙዚቃ መሳርያን እንዳይጫወቱ እና እንዳያዜሙ አፋቸዉን የተያዙት ከያንያን "Festival in the Desert", የተሰኘዉን ዓመታዊ አለማቀፍ የሙዚቃ ድግሳቸዉን ለመቀጠል እና የዓለም ሙዚቃ አፍቃሪዎችን ዳግም ለማሰባሰብ የሚያስችል ተስፋን ፈንጥቆላቸዋል። ሙሉ ቅንብሩን ያድምጡ!
አዜብ ታደሰ
ሂሩት መለሰ