የበርሊን ግንብ የፈረሰበት 30ኛ አመት በጀርመን ተከበረ
ቅዳሜ፣ ጥቅምት 29 2012ጀርመን የበርሊን ግንብ የፈረሰበትን 30ኛ አመት በመላ ሀገሪቱ በመዘከር ላይ ትገኛለች። የጀርመን ፕሬዝዳንት ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር፣ መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል እና የጀርመን ምክር ቤት አፈ- ጉባኤ ዉልፍጋንግ ሾውብለ የበርሊን ግንብ ቅሪት በሚገኝበት ለቀድሞው የምስራቅ ጀርመን መንግሥት ሰለባዎች የመታሰቢያ አበባ አኑረዋል።
ግንቡ ጀርመንን ምሥራቅ እና ምዕራብ ብሎ ለሁለት በከፈለባቸው 40 ገደማ አመታት ከ100,000 በላይ ሰዎች ከምሥራቅ ጀርመን ወደ ምዕራብ ጀርመን ለማምለጥ ሞክረው 5,000 ያክሉ ተሳክቶላቸዋል። በርካቶች በጥበቃ ማማዎች ላይ ባደፈጡ ወታደሮች በተተኮሱ ጥይቶች ተገድለዋል።
በዛሬው ዕለት በበርሊን ብራንደንቡርግ አደባባይ በመካሔድ ላይ በሚገኘው የመታሰቢያ ሥነ-ሥርዓት የፖላንድ፣ ስሎቫኪያ፣ ቼክ ሪፐብሊክ እና ሐንጋሪ መሪዎች ታድመዋል።
የበርሊን ግንብ ተብሎ የሚጠራው እና ምሥራቅ እና ምዕራብ ጀርመንን ለሁለት የሚከፍለው መለያ በይፋ መፍረስ የጀመረው በጎርጎሮሳዊው 1989 ዓ.ም. ነበር።
የጀርመን መራሔ-መንግሥት አንጌላ ሜርክል የቀድሞዎቹን ምዕራብ እና ምሥራቅ ጀርመኖች በቅጡ ለማዋሀድ ከ50 አመታት በላይ ሊወስድ ይችላል ሲሉ ተናግረዋል።
የጀርመን ፕሬዝዳንት ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር ለግንቡ መፍረስ የምሥራቅ አውሮፓ አገሮች ያበረከቱትን አስተዋፅዖ አድንቀዋል።
ፕሬዝዳንቱ «ያለ ፖላንዶች፣ ሐንጋሪያውያን፣ ቼኮች እና ስሎቫኮች ብርታት እና ፍላጎት ሰላማዊው አብዮት እና የጀርመን ውኅደት ባልተሳካ ነበር» ብለዋል።