የስደተኞች ተቃውሞ በቱኒዝያ
ረቡዕ፣ ጥር 29 2005
የሚኖሩት እነዚሁ ተገን ጠያቂዎች የስደተኝነት አቋም እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል። የኮት ዲቯር፡ የቻድ፡ የናይጀሪያ እና የሱዳን ተወላጆች የሆኑት ተገን ጠያቂዎቹ በሊቢያ የተካሄደውን ጦርነት ሸሽተው ነበር ቱኒዝያ የገቡት። ሰላማዊ ሰልፈኞቹ የተመድ በሊቢያ ዓብዮቱ የተጀመረበት ሁለተኛ ዓመት ከሁለት ሣምንታት በኋላ የሚታሰብበትን ምክንያት በማድረግ ለተገን ማመልከቻቸው አዎንታዊ መልስ እንዲሰጥ ተማፅነዋል።
ወይዘሮ ከድጃ ከአራት ሕፃናት ልጆቻቸው ጋ ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ በሹሻ የመጠለያ ጣቢያ ይኖራሉ። ከለበሱት የዩ ኤን ኤች ሲ አር አርማ ከሚታይበት ብርድ ልብስ በስተቀር አንዳችም ንብረት የላቸውም። እሳቸውን የሚያሳስበው ግን ንብረት አልባ መሆናቸው አይደለም።
« እኔ ምግብ ወይም ውኃ ወይም ገንዘብ አይደለም የምጠይቃቸው። ለልጆቼ ከለላ እንዲሰጡልኝ ብቻ ነው። »
የ48 ዓመቷ ከድጃ መላ ቱኒዝያን አቆራርጠው እና እጅግ ረጅም መንገድ ተጉዘው ነው ይህንን ጥያቄዋን ለዩ ኤን ኤች ሲ አር ያሰሙት። የስደተኝነት አቋም እንደማይሰጣቸው የተነገራቸው ወይዘሮ ከድጃ ጦርነቱ ወደ ቱኒዝያ እንድሺሹ ሳያስገድዳቸው በፊት ሊቢያ ውስጥ ተቀጥረው ይሰሩ ነበር።
ልክ እንደሳቸው በሹሹ የመጠለያ ጣቢያ የሚኖሩ እና ለሕልውናቸው መለመን የተገደዱት ሌሎች 212 ተገን ጠያቂዎች ማመልከቻቸው ተቀባይነት ስላላገኘላቸው ተቃውሞ መወጣታቸውን የኮት ዲቯሩ ፍሬድሪክ ገልጾዋል።« ወደ ሊቢያ ልንመለስ አንችልም። ቱኒዝያም ውስጥ መቆየት አንችልም። የተመድ የስደተኞች ጉዳይ ተመልካች መሥሪያ ቤትም አልተቀበለንም። እና ወዴት ነው መሄድ የምንችለው? »
ተገን ጠያቂዎቹ እንደሚሉት፡ ሊቢያ በተለይ ለጥቁር አፍሪቃውያን በጣም አደገኛ ቦታ ናት፡ ምክንያቱም የቀድሞውን የሀገሪቱን መሪ ሙአመር ኧል ጋዳፊን ደግፈዋል በሚል ስለሚወቀሱ። ቱኒዝያ ደግሞ ስደተኞችን ተቀብላ ማስተናገድ የምትችልበት መዋቅር ገና አልተከለችም። ብዙዎች ስደተኞች ለሕይወታቸው ስለሚፈሩ ወደ ትውልድ ሀገራቸው መመለስ አይደፍሩም።
ትናንት በቱኒስ የዩ ኤን ኤች ሲ አር ጽሕፈት ቤት ደጃፍ ሰልፍ ካካሄዱት መካከል አንዱ የዳርፉር ሱዳን ተወላጅ ኦትማን ነው።
« ከሊቢያ ስንሸሽ ተቀብለው ድንኳን ሰርተው አስተናግደውናል፤ ይኸው በዚያ ሁለት ዓመት ከቆየን በኋላ አሁን እንደ ስደተኛ ተቀባይነትን አላገኛችሁም ብለውናል። ለምን? መልሱን የሚያውቁት እነርሱ ብቻ ናቸው።
በቱኒስ ዩ ኤን ኤች ሲአር ን የሚወክሉት የሕግ ባለሙያ ናቢል ቤን ቤክቲ መሥሪያ ቤታቸው በሹሹ መጠለያ ጣቢያ ላሉት ተገን ጠያቂዎቹ ልዩ አስተያየት እንዳደረገ ነው የገለጹት።
« ተገን ጠያቂዎቹ ወደ ትውልድ ሀገራቸው በክብር እንዲመለሱ ለማድረግ ስንል ኃላፊነታችን ከሚፈቅደው እና ከሚጠበቅብን በላይ አልፈን በመሄድ ርምጃ ወስደናል። የመጓጓዣቸውን እና ሀገራቸው ከደረሱም በኋላ አንድ ስራ የሚጀምሩበትን ጥቂት ገንዘብ ለመስጠት ተዘጋጅተናል። »
በሹሹ መጠለያ ጣቢያ ካሉት መካከል ብዙዎቹ በዚህ በተያዘው የየካቲት ወር ወደ ዩኤስ አሜሪካ መሄድ እንደተሳካላቸው የገለጸው ዩ ኤን ኤች ሲአር የመጠለያ ጣቢያውን የፊታችን ሰኔ ለመዝጋት መወሰኑን አመልክቶዋል።
አርያም ተክሌ
ተክሌ የኋላ