የምዕተ ዓመቱ የልማት ግብ ያልተሳካላት ኬንያ
ረቡዕ፣ መስከረም 19 2008ኪንታ አኪኒ ልጇን ልትገላገል ነዉ። ለ19 ዓመቷ ወጣት ይህ ሁለተኛዋ ልጅ መሆኑ ነው።ትንሽ ቆየት ብላም ሴት ልጇን ተገላገለች። ወጣቷ አርግዘዉ በሰላም ከተገላገሉ ኬንያውያን አንዷ ናት። በሀገሪቱ የተደረገ አንድ ጥናት እንደሚጠቁመው በአማካይ በየሁለት ሰዓቱ አንዲት ሴት ከወሊድ ጋር በተያያዘ ኬንያ ውስጥ ትሞታለች። በወሊድ ጊዜ ህይወታቸው የሚያልፍ ሴቶች ቁጥር ከጀርመን ጋር ሲነፃጸር በ70 ከመቶ ከፍ ይላል። አብዛኞቹ ሴቶች ለሞት የሚዳረጉት፤ ከወሊድ በኋላ ብዙ ደም ስለሚፈሳቸው ነው። አምሬፍ አፍሪቃ የተሰኘዉ መንግሥታዊ ያልሁነ ድርጅት ናይሮቢ ዉስጥ በስነተዋልዶና የቤተሰብ ምጣኔ ላይ አተኩሮ ይሠራል። የድርጅቱ የፕሮግራም አስተባባሪና የፅንስና የማህፀን ሀኪም የሆኑት ዶክተር ሺፕራህ ኩሪያ የተሻለ የህክምና አገልግሎት ለማዳረስ ድርጅታቸዉ በብዛት በገጠራማ አካባቢ እና መሠረተ ልማት ባልተስፋፋባቸው አካባቢዎች እንደሚሠራ ገልጸዋል።
« ሴቶቹ የሚሞቱት መከላከል በሚቻሉ ምክንያቶች ነው። የህክምና መሳሪያው ሳይኖረን ቀርቶ አይደለም፤ ለእናቶቹ በቅርበት ባለመገኘታቸው ብቻ ነው። የመሳሪያ አቅርቦቱ ትልቅ ሚና ይጫወታል።»ኪኒታ አኪኒ የመጀመሪያ ልጅዋን የተገላገለችዉ ቤቷ ነበር። ብዙ ደም የመፍሰስ አጋጣሚውም ተፈጥሮ ነበር። አሁን ግን የሶስት ሰዓት የእግር ጉዞ ተጉዛ ነው በአካባቢው የሚገኝ ብቸኛ የማዋለጃ ክሊኒክ የደረሰችው። ምንም እንኳን አንድ ክሊኒክ በአካባቢው ቢኖርም በርካታ ችግሮች እንዳሉ አዋላጅ ዶረን ናሊአካ ያስረዳሉ።
« ወደዚህ ከተዛወርን ጊዜ አንስቶ የውሃ ችግር አለ። አንዳንዴም የሠራተኛ እጥረት አለብን። ይህ ስቃይ ነው። ይሁንና ለእኛ ዋናዉ የእናቶች በጤና መገላገል ነዉ። ሁሉም በሰላም ከተጠናቀቀ፤ ሌላዉ ችግር አይታየኝም።»
ዶረን ናሊአካ በወር 20 የሚጠጉ ነፍሰ ጡሮችን ያዋልዳሉ። የማጉዋና የጤና ማዕከል ከናይሮቢ በስተ ሰሜን በመኪና 12 ሰዓት ከተጓዙ በኋላ የምትገኝ መንደር ናት። ለ40,000 ሰዎች አገልግሎት ይሰጣል። ይሁንና የህክምና አገልግሎቱ በተሻሻለበት እና ወደሀኪም ቤቶች በቶሎ በሚደረስበት አካባቢም እንኳን በርካታ እናቶች ቤት ውስጥ ነውየሚወልዱት ይላሉ፤ ዶክተር ሺፕራህ ኩሪያ « ሌሊት ለምሳሌ የፀጥታ ሁኔታው አስተማማኝ አይደለም። በተለይ በጎስቋላ መንደሮች እናቶች በሌሊት ህክምና ፍለጋ ለመሄድ ምቾት አይሰማቸውም። ምጥ ደግሞ የሚታቀድ ነገር አይደለም። ባልታሰበ ወቅት ነው የሚመጣው። »
ሌላው ችግር ደግሞ በበርካታ የሀገሪቱ ጎሳዎች ዘንድ ልጅ በህክምና ማዕከል መገላገል ባህልን አንዳለመከተል ይታያል። የኬንያ መንግሥት ወደ ጤና ጣቢያ የሚሄዱትን ነፍሰ ጡሮች ለማበረታታት ካለፈው ዓመት አንስቶ በመንግሥት ሆስፒታሎች ነፍሰ ጡሮች በነፃ የሚታከሙበት እና የሚወልዱበት አጋጣቢ አመቻችቷል።
« እንደዚያም ሆኖ አሁን ድረስ ክፍያ የሚጠይቁ ሁኔታዎች አሉ። እናትየዋ ያለችበት ቦታ ለምሳሌ ይወስነዋል። ክሊኒክ የምትሄድበት የመጓጓዣ ገንዘብ ያስፈልጋታል። አንዳንድ ቤተሰቦች በጣም ደሀ ስለሆኑ ይህ ራሱ ትልቅ ጉዳይ ይሆናል። ይህን እና ይህን በመሳሰሉ ችግሮች የተነሳ ኬንያ ከወሊድ ጋር በተያያዘ የሚሞቱትን እናቶች ቁጥር በምዕተ ዓመቱ የልማት ግብ እንደታቀደው በሶስት አራተኛ መቀነስ አልቻለችም።
ሊንዳ ሽታውደ/ልደት አበበ
ሸዋዬ ለገሠ