የምዕራብ ጎንደር ግጭትና የአማራ ክልል መስተዳድር መግለጫ
ዓርብ፣ ጥር 3 2011በያዝነዉ ሳምንት ማክሰኞ በአማራ ክልል ምዕራብ ጎንደር ዞን በገንደ ውሃ ከተማ በተከሰተ ግጭት የሰው ህይወት መጥፋቱ ተገቢ አለመሆኑን የአማራ ክልል ቃል አቃባይ አቶ አሰማኸኝ አስረስ ተናገሩ። አቶ አሰማኸኝ ትናንት ምሽት ላይ ለ«DW» እንደገለጹት የመከላከያ ሰራዊት ህዝቡን ሊያደምጥ ይገባ ነበርብለዋል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ በበኩላቸዉ፤‹‹በውይይትና በትዕግስት ችግሩን ለመፍታት ጥረት አለመደረጉ በእጅጉ አሳዝኖናል›› ‹‹ኃላፊነት የጎደለው፣ ትክክለኛ ያልሆነ እርምጃ ተወስዷል፤ በደረሰው ጉዳት ኃላፊነት መውሰድ ያለበት አካል ኃላፊነት መውሰድ ይኖርበታል፡፡›› ሲሉ ገልፀዋል። በገንደ ውሃ ከተማ የመከላከያ ሰራዊት አባላት ማክሰኞ እለት አመሻሹ ላይ በከፈቱት ተኩስ ቢያንስ ዘጠኝ ሰዎች መሞታቸው እና 15 መቁሰላቸውን የዓይን እማኞች ለ«DW» መግለጻቸው ይታወሳል። ድርጊቱን በመቃወም ረቡዕእለት ሰላማዊ ሰልፍ የወጡት የከተማይቱ ነዋሪዎች በአካባቢያቸው የሰፈረው የመከላከያ ሰራዊት ከስፍራው ለቅቆ እንዲወጣ ጠይቀዉም ነበር። በምዕራብ ጎንደር ስለነበረዉ ግጭትና ስለአማራ ርዕሰ መስተዳድር አቋም የአማራ ክልል ቃል አቃባይ አቶ አሰማኸኝ አስረስ ትናንት ምሽት ላይ ከ«DW» ጋር ያደረጉት ሙሉ ቃለምልልስ እነሆ።
አዜብ ታደሰ
አርያም ተክሌ