የምዕራብ ጉጂ ዞን ግጭት ረግቧል
ረቡዕ፣ ሚያዝያ 17 2010እንዲያም ሆኖ በግጭቱ የተፈናቀሉትና በሽዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች በተጠለሉበት ቦታ የሚያገኙት ርዳታ በቂ እንዳልሆነ እና በተለይ ሕጻናት እና ነፍሰጡት እናቶች እንግልት ላይ መሆናቸዉን ተናግረዋል። ምዕራብ ጉጂ ዞን በቀርጫ፣ በቡሌ ሆራ፣ በብርብርሣ ኮጆአ፣ በሻኪሶና በሐንባላ ዋማና ወረዳዎች የሚኑሩ የጌዴኦ ብሔር ተወላጆች ማንንነትን መሠረት ባደረገ ግጭት ሰዎች መሞታቸውን፤ መቁሰላቸውንና በሺሕዎች የሚቆጠሩ መሰደዳቸውን ለዶይቼ ቬለ መረጃዉን ያደረሱ የዓይይን እማኞች በአሁኑ ወቅት በአካባቢዉ ግጭቱ መቆሙንና ነዋሪዉ ቀስ በቀስ እየተመለሰ ይናገራሉ። ችግሩ ያለዉ በአምስት ወረዳዎች ላይ ነዉ ያሉት የአካባቢዉ ነዋሪ አቶ ታደሰ ኪፔ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ነዋሪ መፈናቀሉን ገልፀዋል።
የአካባቢዉ ነዋሪ በግብርና እንደሚተዳደር እና በተለይ ቡና እና የእንሰት ምርትን እንደሚያመርት የተናገሩት አቶ ታደሰ ኪፔ መንግሥት የጠፋዉን ንብረት እንደሚመልስ ለአካባቢዉ ነዋሪዎች መናገሩንም አክለዋል። ተፈናቃዮች ወደ መኖርያ ቀያቸዉ እየተመለሱ ናቸዉ ሲሉ የገለፁልንና ለደኅንነታቸዉ ሲባል ማንነታቸዉን እንዳንገልጽ የጠየቁን ሌላኛዉ የአካባቢዉ ነዋሪ በስፍራው ላይ አሁንም ዉጥረት እንዳለ አመልክተዋል።
በመንግሥት በኩል የሚሰጠው ምላሽ በጣም የዘገየ ነዉ ያሉት ነዋሪዉ ፤ ተፈናቃዮቹ የሚሰጣቸዉን ምግብ አብስለዉ የሚበሉበት እንኳ ቦታ አላገኙምም ብለዋል። በጉጂ ዞን ይህ አይነቱ ከፍተኛ ጥቃት ባለፉት 20 እና 25 አመታት ሲከሰት ይሄኛዉ ለአራተና ጊዜ ነዉ ሲሉ የተናገሩት ነዋሪዉ ፤ ወደ መኖርያ ቀያቸዉ እየተመለሱ ያሉት ተፈናቃዮች ዳግም ሌላ ጥቃት እንዳይደርስባቸዉ ከለላ እንዲሰጥ ተማፅነዋል።
ሁኔታዎችን ለማረጋገጥና በመንግሥት ወገን ያለዉን ሁኔታ ለመጠየቅ በተደጋጋሚ የደወልንላቸዉ የጌድዮ ዞን ኮሚዩኒኬሽን ተጠሪ አቶ ታሪኩ በየነ ከቦን ስቱድዮ ስንደዉልላቸዉ ስልካቸዉ ላይ የሚያዩት ቁጥር የሀገር ዉስጥ የሞባይል ስልክ ቁጥር በመሆኑ ደጋግመው ከዋና ቢሯዋችን እንድንደውልላቸው ከጠየቁን በኋላ በመጨረሻ መረጃዉን ለእናንተ ለመስጠት ኮማንድ ፖስቱን ማሳወቅ ይኖርብኛል ሲሉ በአጭሩ መልሰዉልናል።
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ