የምርጫ ዝግጅትና ተቃዉሞ በግብፅ
ዓርብ፣ ሚያዝያ 26 2004የፀጥታ ኃይሎች ላይ ድንጋይ ወርዉረዋል፤ የመንግስት ኃይሎችም በአፀፋዉ ድንጋዩን መልሰዉ ከመወርወር ባሻገር ሰልፈኞቹን በዉሃ ሊበትኑ መሞከራቸዉ ተገልጿል። የመንግስት ባለስልጣናትም አራት ሰዎች መቁሰላቸዉን አመልክተዋል። ሸዋዬ ለገሠ
ግብፅ ዉስጥ ወታደራዊዉ ምክር ቤት አሁንም ስልጣን ላይ የሚገኘዉ አካል ነዉ። በግንቦት ወር ማለቂያ ከሚካሄደዉ ምርጫ በኋላ ሁኔታዉ በዚህ ሊቀጥል እንደማይችል የሚገምቱ ቢኖሩም፤ የፖለቲካ ተንታኞች በአንፃሩ ወታደራዊዉ አመራር ስልጣኑን ያስረክባል የሚለዉን ይጠራጠራሉ። ዛሬ ሰልፍ የወጡት የወታደራዊዉ ምክር ቤት ከስልጣን አለመዉረድ ተቃዋሚዎች ሙባረክን ከስልጣን ካስለቀቀዉ ህዝባዊ አመፅ ማግስት ይደረጋል የተባለዉ ምርጫ ዘግይቷል፤ ስልጣን የያዙት ጀነራሎችም ሊለቁ አልተዘጋጁም የሚል ትችት ሰንዝረዋል።
ረቡዕ ዕለት በመከላከያ ሚኒስቴር አቅራቢያ ከተካሄደዉና የሰዎችን ህይወት ከተጠፋበት የተቃዉሞ እንቅስቃሴ ማግስት ትናንት ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ለመስጠት ከቀረቡት ሶስት ጀነራሎች አንዱ ማህሙድ አል አሰር ወታደራዊዉ ምክር ቤት ስልጣን ይዞ የመሰንበት እቅድ እንደሌለዉ፤ ነፃ ምርጫ እንዲካሄድም ዝግጁ ነዉ ብለዋል። አያይዘዉም በህዝባዊዉ ዓመፅ ወቅት ሠራዊቱ ከህዝቡ ጎን እንደነበር አስታዉሰዋል፤
«ፕሬዝደንት ሙባረክ ስልጣን ላይ በነበሩበት ወቅት ወታደሩ ከግብፅ ህዝብ ጎን እንደነበር ላስታዉሳችሁ እፈልጋለሁ። ሁሌም ከሰላማዊ ሰልፈኞች ጎን ነበር የቆምነዉ፤ በተጨማሪም መቼም ቢሆን ህዝቡ ላይ የኃይል ርምጃም እንደማንወስድ ቃል ገብተናል።»
ረቡዕ ዕለት ከምርጫዉ የታገዱት ሳላፊስት ፖለቲከኛ ሃዚም አቡ ኢስማኢል ደጋፊዎች ላይ በመከላከያ ሚኒስቴር አካባቢ ያልታወቁ ጥቃት አድራሾች በወሰዱት የኃይል ርምጃ ጉዳት ደርሷል። ጀነራሉበወቅቱህይወታቸዉንላጡትእናለተጎዱትየተሰማቸዉንሃዘንምገልፀዋል፤
«ትናንት በተከሰተዉ አጋጣሚ ህይወታቸዉን ላጡትና ጉዳት ለደረሰባቸዉ የተሰማንን ሃዘንን በወታደራዊዉ ከፍተኛ ምክር ቤት ስም ሃዘኔን እገልፃለሁ። በዚህ አጋጣሚ የግብፃዉያን ደም እጅግ ክቡር መሆኑን ልገልፅ እፈልጋለሁ። መፍሰስ የሚገባዉም ሐገራቸዉን በመከላከል ተግባር ላይ ብቻ መሆን አለበት።»
ከካይሮ ከተማ በተጨማሪ አሌክሳድሪያም እንዲሁ ወደ2,000 የተገመቱ ሰልፈኞች አደባባይ መዉጣታቸዉ ተገልጿል። ጄነራል አሰር ግን ግብፅ አደጋ አንዣቦባታል ባሉበት በዚህ ወቅት የአገር ዉስጡ የአመፅ እንቅስቃሴ እልባት እንዲያገኝ አሳስበዋል፤
«ግብፅ አደጋ ላይ ናት። እንዲህ ባለዉ አጋጣሚ የተቃዉሞዉ ሰልፍ ለእኛ መልካም አይደለም። እያንዳንዱ እዉነተኛ ግብፃዊ በፖለቲካዉም ይሁን በኤኮኖሚ፤ ወይም በወጣትነት ይህን አደጋ ሊዋጋዉ ይገባል።»
ምንም እንኳን ለህዝቡ መግለጫ ለመስጠት የቀረቡት ወታደራዊ መኮንኖች የግብፅ ወታደራዊ መኮንኖች ስልጣን ላይ የመቆየታቸዉ አባዜ ከሙባረክ ዘመን አንስቶ የተለመደ ነዉ ባዮቹ ተቃዋሚዎች በበኩላቸዉ ወታደራሚዉ ምክር ቤት በግንቦት ወር ማለቂያ ስልጣኑን ለተመረጠዉ ህዝባዊ አካል እንዲያስረክብ ዛሬም ሲጠይቁ አርፍደዋል። የግብፅ ፕሬዝደንታዊ ምርጫ ለግንቦት 15 እና 16፤፤ ዳግም የመለያ ምርጫዉ ደግሞ ለሰኔ 9 እና 10 2004ዓ,ም ነዉ የተቀጠረዉ።
ሸዋዬ ለገሠ
ሂሩት መለሰ