«የማፑቶ ዉል» በአስር ዓመት ምን ተሰራ?
ረቡዕ፣ መስከረም 8 2006በዚህ አካባቢ የሚገኙ ድሆች የማህበረሰብ አባላት፤ ለችግር ግዜ ያስቀመጡትን ምግብ ተጠቅመዉ በመጨረሳቸዉ ለእለት ጉርሳቸዉ፤ ገበያ የቀረበዉን ዉድ ምግብ መግዛት ተገደዋል ሲል ድርጅቱ አስታዉቋል። ለአካባቢዉ አነስተኛ ገበሪዎች እና አርብቶ አደሮች እርዳታ እንዲያደርግላቸዉ ድርጅቱ ለዓለማቀፉ ማህበረሰብ ጥሪዉን አቅርቦአል። የረሃብ አደጋ የተሠማዉ ዓመት የአፍሪቃ ሕብረት አባል አገሮች የግብርና መስክን በመደገፍ ረሃብን ለመዋጋት ማፑቶ ሞዛምቢክ ዉስጥ የተፈራረሙት ዉል 10 ዓመትን በደፈነበት ወቅት መሆኑ ነዉ። በአነስተኛ ግብርና ዘርፍ የተሰማሩ የሳህል አካባቢ ገበሪዎች ለክፉ ግዜ አስቀምጠዉት የነበረዉን እህል ተጠቅመዉ በመጨረሳቸዉ፤ አስጊ ሁኔታ ላይ ይገኛሉ። ከዚህ ከባድ ችግር ሌላ፤ በአካባቢዉ ላይ የሚታየዉ ከፍተኛ የአየር መለዋወጥ ሁኔታዉን አስከፊ ደረጃ ላይ እንዳደረሰዉ፤ ዋና ጽ/ቤቱን በጋና ያደረገዉ የአፍሪቃ የተመ የምግብ እና የእርሻ ድርጅት ባልደረባ ጀምስ ቴፍት ተናግረዋል፤« እጅግ አስጊ እና አደገኛ አይነት የግብርና ዘዴ ነዉ። የዉሃ እጥረት አለ። ይሄ ደግሞ ማንኛዉንም ያልታሰበ ጉዳይ ወደ ችግር ሊያመራ ይችላል። የምግብ እህል ዋጋ እየተቀያየረ በመጣ ቁጥር ደግሞ ከእጅ ወደ አፍ ለሚኖሩ ማህበረሰቦች ሁኔታዉ እጅግ አስከፊ እየሆነባቸዉ ነዉ»በአፍሪቃ ከሚኖረዉ ሕዝብ ከአምስት አራቱ በግብርና ነዉ የሚተዳደረዉ። የነዋሪዉ ቁጥር እየጨመረ በሚሄድበት ህብረተሰብ ዉስጥ፤ የተሟላ የምግብ አቅርቦት እንዲኖር፤ የምርቱ መጠን መጨመር ይኖርበታል። በዚህ ረገድ የአፍሪቃ ሕብረት፤ በአህጉሪቱ የሚታየዉን የረሃብ አደጋ ለመቅረፍ «የማፑቶ ዉል» በሚል ስምምነትን ካፀደቀ ዘንድሮ አስር ዓመቱን ደፈነ። ሀገራቱ በዛሪ አስር ዓመቱ እቅዳቸዉ መሰረት፤ ካላቸዉ በጀት ቢያንስ 10 ከመቶዉን ወጭ በግብርና ላይ ለማዋል ነበር። ከዚህ ጋር ተያይዞ ሀገራቱ በግብርናዉ ዘርፍ ምርት በየዓመቱ 6% እድገትን አሳይተዋል። እዉነታዉ ግን የማፑቶ ዉል፤ ከተደረሰ ከ 10 ዓመት በኋላ ዛሪም፤ እቅዱ ላይ መድረስ አለመቻሉን ነዉ። የአፍሪቃ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ንኮዛሳ ድላሚኒ ዙማ፤ ከ 54 የአፍሪቃ ሕብረት አባል ሀገራት መካከል፤ 10 ሀገራት፤ 10% እድገትን ማሳየታቸዉን ገልጸዋል። ሀገራቱ አስገኙት የተባለዉን የእድገት መጠን፤ ከቁጥሩ ሌላ እንብዛም የሚታይ ነገር አለመኖሩን መንግስታዊ ያልሆነዉ /Brot für die Welt/ ማለትም ዳቦ ለዓለም የተሰኘዉ የወንጌላዊት የልማት ሥራ ድርጅት ባልደረባ ፍራንኮ ማሪ ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪ የምርቱን ጥራትም ማየት ያስፈልጋል፤ ባይ ናቸዉ፤« ብዙ ገንዘብ መኖሩ ብቻ የችግሩ መፍትሄ ሊሆን አይችልም። ለምሳሌ ጋናን ብንወስድ በግብርናዉ ዘርፍ በዓመት 10 % እድገት ካስገኙት የአፍሪቃ ሀገራት ትመደባለች። በጋና ከፍተኛዉ የመንግስት በጀት በግብርና ቴክኖሎጂ ልማት ላይ ያተኮረ ነዉ። ይኸዉም ገበሪዎች በትራክተር እንዲጠቀሙ ለማበረታት ከመንግስት ገንዘብ የሚሰጥበት ግብርና መረሃ-ግብር አለቸዉ። እንዲህ አይነቱ አሰራር በአፍሪቃ አብዛኛዉን ግዜ አጥጋቢ አይደለም፤ ለምሳሌ አነስተኛ እርሻን ማለት ሁለት ሄክታር የእርሻ መሪትን በትራክተር ማረሱ ብዙ ጥቅም አያስገኝ»
እንደ ፋራንኮ ማሪ በአፍሪቃ ያለዉን ማህበረሰብ ፍላጎት ለማሟላት፤ የአፍሪቃ ሕብረት ትናንሽ ገበሪዎች ለምርታማነት እንዲበቁ ማገዝ ይጠበቅበታል። ከዚህ በተጨማሪ የተለያየ የአፍሪቃ ሀገሮች አህጉራዊ ግብይት መገንባት ይኖርባቸዋል። ባለፈዉ ዓመት የአፍሪቃ መንግስታት መሪዎች፤ አዲስ አበባ ኢትዮጵያ ላይ ባደረጉት ስብሰባ በአፍሪቃ የሚታየዉን የረሃብ ችግር ለማጥፋት የተጀመረዉ ትግል ግብ እንዳልደረሰ መግለፃቸዉ ይታወሳል። አፍሪቃ መሪዎች ይህንን ሲያስታዉቁ አህጉሪቱ ከዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር በመጣመር ጎ,አ እስከ 2025 ዓ,ም ድረስ የረሀብን ችግር ከአህጉሪቱ ለማጥፋት እቅድ መያዛቸዉን ተናግረዋል። ከዓለማቀፍ አጋር ድርጅቶች መካከል የብራዚሉ የዓለም አቀፍ የምግብ ድርጅት ተቋም ይገኝበታል። ሕብረቱ መጭዉን የጎ 2014 ዓ,ም የግብርና እና የምግብ ዋስትና የሚረጋገጥበት ዓመት ሲል ሰይሞአል።
አዜብ ታደሰ
ነጋሽ መሃመድ