የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ተሿሚዎችን ብቁነት መመርመር ይችላሉ?
ዓርብ፣ ሐምሌ 28 2009የኢትዮጵያ የትምህርት ሚኒሥቴር በሶስት አመታት ውስጥ ሶስተኛ ሚኒሥትር ተሾመለት። ከኅዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በአጠቃላይ ትምህርት ዘርፍ በምኒስትር ድኤታነት ሲያገለግሉ የቆዩት ዶ/ር ጥላዬ ጌቴ አምባዬ የትምህርት ሚኒስትር ሆነዋል። በሚኒሥትር ማዕረግ የገቢዎች እና ጉሙሩክ ባለሥልጣንን ሲመሩ የከረሙት አቶ ከበደ ጫኔ የፌደራል ጉዳዮችና አርብቶ አደር አካባቢ ልማት ሚኒስቴር ሚኒስትር ሆነዋል። በምትካቸው አቶ ሞገስ ባልቻ በሚኒስትር ማዕረግ የገቢዎች እና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሆነው ተሾመዋል።
የመንግሥቱን የሹመት ጥያቄ በሙሉ ድምፅ ካጸደቁት የምክር ቤት አባላት መካከል ሌላ ጥያቄ ያላቸው አልጠፉም። የምክር ቤቱ አባላት በጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሹመት ስለሚታጩ ግለሰቦች ተጨማሪ መረጃ ለማሰባሰብ ማብራሪያ ፈልገዋል። በኢትዮጵያ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ፅ/ቤት የመረጃ ባለሙያው አቶ ናምሴ አልቃ "አንዳንድ አባላት የተሿሚዎች የህይወት ታሪክ ብቻ ሳይሆን እንዴት ሰሩ የሚሉበት ሁኔታ ቢኖር" ብለው መጠየቃቸውን ተናግረዋል።
በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አስመላሽ ወልደስላሴ አስፈላጊ ከሆነ በአሰራሩ ላይ ወደ ፊት ክርክር ሊካሔድ እንደሚችል ለምክር ቤቱ አባላት ተናግረዋል። የምክር ቤቱ አባላት ፍላጎት በእርግጥም የእጩ ተሿሚዎቹን አቅም እና ተገቢነት ለመፈተሽ አሰራሩ እንደማይፈቅድ ታዛቢዎች ይተቻሉ። "የሚሾሙት ሰዎች ታሪክ አስቀድሞ ቢሮ ድረስ ተልኮ በኮሚቴ ደረጃ ታይቶ በራስ ሰራተኛ ተመርምሮ ይመጥናሉ አይመጥኑም" የሚለው ሊታይ እንደሚገባ የሚናገሩት የሕግ ባለሙያው አቶ ሙሉጌታ አረጋዊ ናቸው። አቶ ሙሉጌታ "የምክር ቤቱ አባላት የአንድ ፓርቲ አባላት ናቸው። የመረጃ ምንጫቸው የራሳቸው ፓርቲ ነው። ከየት ነው መረጃ የሚያመጡት? ከፓርቲያቸው ውጪስ ማውራት እና መወሰን ይችላሉ ወይ?" ሲሉ የሚገጥማቸውን ፈተና ያጠይቃሉ።
የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ መንግስት የትምህርት ሚኒስትር የነበሩት ዶ/ር ሽፈራው ተክለማርያምም ይሁኑ የፌደራል ጉዳዮችና አርብቶ አደር አካባቢ ልማት ሚኒስትር ሆነው ያገለገሉት አቶ ካሳ ተክለብርሃን ለምን ከቦታቸው እንደተነሱ በይፋ ያለው ነገር የለም። የሁለቱን ሚኒስትሮች ሹመት ያጸደቀው የተወካዮች ምክር ቤትም ለምን ብሎ ስለመጠየቁ መረጃ የለም። የቀድሞው የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ፕሬዝዳንት አቶ ልደቱ አያሌው የቁጥጥር እና ክትትል ሥርዓት በመንግሥታዊ መዋቅሩ ውስጥ ጠፍቷል ሲሉ ይተቻሉ።
"አንድ ፓርቲ መቶ በመቶ ምርጫን አሸንፊያለሁ ካለ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ የክትትል የቁጥጥር አሰራር አይኖርም። ይኼ ኢትዮጵያ ውስጥ ዴሞክራሲ ምን ያህል ችግር ውስጥ እንደሆነ እንዳልሰራ፤ ዴሞክራሲ ባለመኖሩ ደግሞ የአገሪቱ አስተዳደር ችግር ውስጥ እንደሆነ ነው የሚያሳየው።"
የዛሬው የተወካዮች ምክር ቤት ጉባኤ ሹመት ሲያጸድቅ ያለ መከሰስ መብትምንም ገፏል። 26.2 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጡ ጨረታዎች በውድድር ላልተካፈሉ ኩባንያዎች ሰጥተዋል 500,000 ብር ጉቦም ተቀብለዋል የሚል ክስ የቀረበባቸው የፋይናንስ እና ኤኮኖሚ ትብብር ሚኒሥትር ድኤታ አቶ አለማየሁ ጉጆ ያለመከሰስ መብት በምክር ቤት ተገፏል።
እሸቴ በቀለ
አርያም ተክሌ