1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

«ከነጻ አውጭነት ወደ አምባገነንነት»

ሐሙስ፣ ግንቦት 17 2015

«እጅግ በጣም ተስፋ የተጣለበት ጊዜ ነበር። በደርግ ዘመነ መንግስት ኤርትራ ውስጥ የመኖር ተስፋቸው ተሟጦ እና ለደህንነታቸው ሰግተው ሀገር ጥለው ሸሽተው የነበሩ ሁሉ ከአሜሪካ ፣ ካናዳ ፣ ስዊዲን ፣ ኖርዌይ እና አውሮጳ ውስጥ የነበሩ ሰዎች ሁሉ ወደ ኤርትራ መትመም ጀምረው ነበር። በዚም በኢንቨስትመንት ለመሰማራትም ፍላጎቱም ከፍተኛ ነበር።»

https://p.dw.com/p/4Rp59
Isaias Afwerki
ምስል Khalil Senosi/AP Photo/picture alliance

30 ዓመታትን በስልጣን ላይ ያሉት ኢሳያስ አፈወርቂ ከየት ወዴት ?

ኤርትራን ከሶስት አስርት ዓመታት በላይ መርተዋል። ሀገራቸው በይፋ ነጻነቷን ያወጀችበትን ሰላሳኛ ዓመት ትናንት በአደባባይ ለህዝባቸው ንግግር በማድረግ እንኳን አደረሳችሁም ብለዋል። ያለአንዳች ተቀናቃን ሰላሳ ዓመታትን ከተቆናጠጡበት ስልጣናቸው እንዳሉ ዛሬም አሉ። ነገር ግን ትናንት ትግሉን መርተው ነጻ ሀገር የመሰረቱት እኚያ የነጻነት አባት ተብለው ይታወቁ የነበሩት ኢሳያስ አምባገነንነታቸው ከፍ ብሎ ይሰማላቸዋል። የተገለለች እና ሚስጢራዊት ሀገር ፈጥረዋል  ተብለውም ይወቀሳሉ። ከነጻ አውጭነት ወደ ጨቋኝነት ተሸጋግረዋል ስለተባሉት ፕሬዚዳንት ኢሳያስ የኢሳቅ ካልዴዚን ዘገባ ታምራት ዲንሳ አዘጋጅቶታል።

ከሶስት አስርት ዓመታት በላይ ኤርትራን በፕሬዚዳንትነት የመሯት ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ከነጻነት አባትነት ወደ ለየለት አምባገነን የተቀየሩ መሪ በማለት ምዕራባውያኑ ብርቱ ትችት እና ወቀሳ ያቀርቡባቸዋል። ኤርትራ ከኢትዮጵያ ለመገንጠል በወቅቱ ኢሳያስ በሚመሩት የኤርትራ ነጻነት ግንባር ወይም ሻዕቢያ  እና ደርግ መካከል ሲደረግ የነበረውን ደም አፋሳሽ ጦርነት በመዘገብ የምትታወቀው እንግሊዛዊቷ ጋዜጠኛ እና ደራሲ ሚኬላ ሮንግ ኤርትራ ከኢትዮጵያ ነጻነቷን ተቀዳጅታ ስትገነጠል በሀገር ውስጥም ሆነ በውች ለሚገኙ ኤርትራውያን አዲስ ተስፋ ያጫረ ጊዜ እንደነበር ታስታውሳለች። የኢትዮጵያ እና የኤርትራን ግንኙነት የማጠናከር ጥረት 
«እጅግ በጣም ተስፋ የተጣለበት ጊዜ ነበር። በደርግ ዘመነ መንግስት ኤርትራ ውስጥ የመኖር ተስፋቸው ተሟጦ እና ለደህንነታቸው ሰግተው ሀገር ጥለው ሸሽተው የነበሩ ሁሉ ከአሜሪካ ፣ ካናዳ ፣ ስዊዲን ፣ ኖርዌይ እና አውሮጳ ውስጥ የነበሩ ሰዎች ሁሉ ወደ ኤርትራ መትመም ጀምረው ነበር። በዚም በኢንቨስትመንት ለመሰማራት እና ከውጭ ሃገራት ባመጧቸው ክህሎቶች ወደ ስራ የመግባት ፍላጎቱም ከፍተኛ ነበር።» 
ኤርትራ በይፋ ከኢትዮጵያ ተገንጥላ ራሷን የቻለች ሀገር መሆኗ በይፋ ከታወጀ ትናንት ግንቦት 16 ቀን 2015 ዓ/ም ድፍን 30 ዓመታት ሞላው። አዲሱ የኤርትራ ትውልድ አንድ መሪ ፣ አንድ የፖለቲካ ፓርቲ ብቻ ነው የሚያውቀው። ፕሬዚዳንት ኤሳያስ አፈወርቂ ነጻ ያወጧትን ሀገር እርሳቸው ብቻ የሚመሩባት የእርሳቸው ፓርቲ ብቻ መንግስት የሆነበት ሀገር ይዘው ቀጥለዋል። ኤርትራ አሁን በብዙ መልኩ የምትገለጥ አገር ሆናለች የሚሉ በርካቶች ናቸው ። አንዳንዶች ከዓለም የተነጠለች ፤ አንዳንዶች የአፍሪቃ ሰሜን ኮሪያ ፣ ሌሎቹ ደግሞ ሌላ ። የሆኖ ሆኖ ፕሬዚዳንት ኢሳያስን በፍጹም አምባገነንነት ከሚፈርጇቸው የምዕራቡ ዓለም የምተመጣው ጋዜጠኛ ሚኬላ ለኢሳያስ የአምባገነንነት ዘመን መጀመሪያ የኢትዮ ኤርትራን ጦርነት በምክንያትነት ትጠቅሳለች።
«ለነገሮች መለወጥ ዋና ምክንያት የነበረው በባድመ ጉዳይ ላይ የተቀሰቀሰው የ1991ዱ የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ነው። ነገር ግን ሊሰመርበት የሚገባው ነገር  ከባድመው ጦርነት ጀርባ ሌሎች  ውጥረት ቀስቃሽ ነገሮች እንዳሉ ነው። የኤኮኖሚ ጉዳይ አለ፤ የሀገሪቱ የወደፊት ዕጣን የሚመለከተው ጉዳይም አንዱ ነው። »
 ከዚህ በኋላ ነው ትላለች ጋዜጠኛ እና ደ,ራሲ ሚኬላ ሮንግ አቶ ኢሳያስ ተቀናቃን እንዳይነሳባቸው ዙሪያቸውን ማጽዳት የጀመሩበትን አጋጣሚ ወደ ኋላ መለስ ብላ የምታስታውሰውን የምትናገረው።ዐቢይ «ኢትዮጵያዊያን ያልሆኑ» ያሏቸው ማን ናቸው?
በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን ህይወት የቀጠፈው የኢትዮ ኤርትራው ጦርነት በሁለቱ ሃገራት ላይ ካደረሰው ሰብአዊ እና ቁሳዊ ውድመት ባሻገር ኤርትራ ነጻ ባወጣቻቸው ሰው አገዛዝ ስር ወ,ድቃ እድትቀር መንገድ መጥረጉን ትጠቅሳለች።
የአፍሪቃ የደህንነት ጉዳዮች ተንታኝ ፊደል አማክዬ ኦውሱ እንደሚሉት ደግሞ ኢሳኢስ የመሪነት ዘመናቸው ስልጣናቸውን በማጠናከር ላይ ብቻ ያተኮረ እንደነበረ ይገልጻሉ።
«በወቅቱ ጥሩ ነበሩ ወይስ አይደለም ብለን የጠየቅን እንደሆነ በሰብአዊ መብት ረገጣ ውስጥ ገብተው እናያቸዋለን።  በርካታ ኤርትራውያን ተቃዋሚዎች ወይም ኤርትራን ለቀው የተሰደዱ ሰዎች ምክንያታቸው ውስጣዊ ግጭት ሳይሆን ከአምባገነን አገዛዝ ሽሽት ነው።»
  በኤርትራ የኃይማኖት ነጻነቱ መገደቡን የሚናገሩት እነዚሁ አስተያየታቸውን ለዶይቼ ቬለ የሰ,ጡ ባለሞያዎች የቴክኒክ ኮሌጆች እና ዩኒቨርሲቲውም ወደ ወታደራዊ የቴክኒክ ማስተማሪያነት መቀየራቸውን ይገልጻሉ ። 
የደህንነት ጉዳዮች አጥኚው አዉሱ ሂደቱ ኤርትራን የተነጠለች ሌላዋ ሰሜን ኮሪያ  በአፍሪቃ ምድር ፈጥሯል ይላሉ ።
«ኤርትራን የተመለከትን እንደሁ ሰሜን ኮሪያ ለተቀረው ዓለም ምን ማለት እንደሆነች አይነት ኤርትራም የአፍሪቃ ሌላዋ  ገጽታ ማለት ናት ። ሚስጥራዊ ናት ፣ ተገላለች »
የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ የነጻነት ቀኑን አስመልክተው ትናንት በአደባባይ ለህዝብ ባደረጉት ንግግራቸው ዓለማቀፋዊ የበላይ ያሏቸው አሜሪካ እና አጋሮቿ በኤርትራውያን ነጻነት እና በኢትዮጵያ እና ኤርትራ መካክል ልዩነት የመፍጠር ስልትን ሲከተሉ ነበር በማለት ከሰዋል። 
« በዋናናነት ዋሽንግተን እና አጋሮቿ ባለፉት ሰማንያ ዓመታት ነጻነታችንን በመቃወም ፣ ያለፉትን ሶስት አስርት ዓመታት ደግሞ ትውልድን በማጋጨት እንዲሁም  በኢትዮጵዮያ እና ኤርትራ መካከል ጦርነት ለመቀስቀስ ያለማቋረጥ ልዩነት የመፍጠር ስልትን ይከተሉ ነበር ። ነገር ግን ይህ ስልታቸው አለመሳካቱ የታየ ተጨባጭ እውነታ ነው  »የኤርትራው ፕሬዝዳንት የቻይና ጉብኝት አንደምታ
ፕሬዚደንቱ በትናንትናው ሰፋ ባለው ንግግራቸው ባለፉት አምስት ዓመታት በአዲስ ምዕራፍ ውስጥ መግባቷን አመልክተው ነገር ግን ሀገራቸው የጀመረቻቸውን መልካም ጅምሮች የሚያሰናክሉ በሶስት ምዕራፎች የተከፋፈሉ ያሏቸው የውክልና ጦርነት በአሜሪካ እንደተከፈተባቸው ተናግረዋል። ምንም እንኳ የጦር ኃይላቸው ሁሉንም በአሸናፊነት መወጣቱን አያይዘው ቢገልጹም ። 
ፕሬዚዳንት ኢሳያስ በኤርትራ ነጻነት በዓል ላይ ምዕራባውያኑን ተችተው ንግግር  በቻይና ይፋዊ የስራ ጉብኝት አድርገው ከተመለሱ በኋላ ነው።  

ታምራት ዲንሳ

አዜብ ታደሰ