ኢትዮ ቴሌኮምና የ4G ቴክኖሎጂ
ዓርብ፣ ነሐሴ 2 2006የቴሌኮም አገልግሎት የተገልጋዮችን ልብ የሚያረካ እንዳልሆነ ተጠቃሚዎች ደጋግመዉ የሚገልፁት ጉዳይ ነዉ። ኢትዮ ቴሌኮም በቅርቡ በሰጠዉ መግለጫም አሉ የሚባሉትን ችግሮች የሚያስተካክሉ ፕሮጀክቶችን ቀይሶ በመንቀሳቀስ ላይ መሆኑ አመልክቷል። 4 G ወይም አራተኛዉ ትዉልድ የተሰኘዉ ቴክኖሎጂ ጠቀሜታና ኢትዮጵያ ልትወስድ የሚገባቸው ጥንቃቄዎች ምን ምን ናቸው? ቴክኒዎሎጂዉን የሚያዉቁስ ምን ይላሉ? ኢትዮጵያ ለቻይናዎቹ ሁዋዊና ዜድ ቲኢ የቴሌኮም ኩባንያዎች ከሰችጠው የ1.6 ቢሊዮን ዶላር የቴሌኮም ማስፋፊያ ፕሮጀክት ውስጥ በአዲስ አበባ ኔትወርክ ማስፋፊያና የአዳዲስ አገልግሎቶች ዝርጋታ ተጠናቆ ለአገልግሎት ዝግጁ ነው ሲል ኢትዮ ቴሌኮም አስታውቋል። በሀገሪቱ በብቸኝነት የቴሌኮም አገልግሎትን የሚያቀርበው ኢትዮ ቴሌኮም በአንድ ወር ውስጥ የ4G አገልግሎትን ለ400 ሺ ደንበኞች ሊያቀርብ በዝግጅት ላይ ነው። ከጥቂት ዓመታት በፊት በዓለም አቀፍ ደረጃ ሥራ ላይ የዋለው ይህ ቴክኖሎጂ ውድ ቢሆንም በአገልግሎት አሰጣጡ ለውጥ እንደሚያመጣ በበርሊን ቴክኒካል ዩኒቨርሲቲ የማስተርስ ተማሪ የሆኑት አቶ ቴዎድሮስ ተሰራ ይናገራሉ።የኢትዮጵያ የቴሌኮም አገልግሎት በቅሬታዎች የታጀበ ነው። የኢትዮ ቴሌኮም የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አብዱራሂም አገልግሎቱ የገጠሙትን ችግሮች አዲሱ የቴሌኮም ማስፋፊያ እንደሚፈታቸዉ ይህን ጉዳይ አስመልክተዉ በሰጡት መግለጫ በቅርቡ እንዲህ ገልጸዉ ነበር።
የቴሌኮም ቴክኖሎጂ እድገትን ተከትሎ በሚደረግ የአገልግሎት ለውጥ አዲሱ ከቀደመው ጋር ተመጋጋቢ ሊሆን ይገባል የሚሉት አቶ ቴዎድሮስ ተሠራ ይህን ማድረግ ካልተቻለ ኪሳራ ያስከትላል ሲሉም ያስጠነቅቃሉ።
ከአዲሱ የቴሌኮም ማስፋፊያ የሚጠበቀውን አገልግሎት ለማቅረብ የቴክኖሎጂው የጥራት ደረጃ መቆጣጠር፤ ኢትዮጵያውያን ባለሙያዎችን ማሰልጠንና የመንገድ፤ መብራት፤ ውኃና ፍሳሽ ሥራዎችን ከሚያከናውኑ ተቋማት ጋር በመግባባት በመሥራት መሠረተ ልማቱን ከብልሽት መጠበቅ አስፈላጊ ነው ሲሉ አቶ ቴዎድሮስ ተሰራ ተናግረዋል።
እሸቴ በቀለ
ሸዋዬ ለገሠ