አዲስ አበባ ፈጣን የኢንተርኔት አገልግሎት ልታገኝ ነዉ ተባለ
ማክሰኞ፣ ግንቦት 2 2014ማስታወቂያ
ኢትዮ-ቴሌኮም ዓለም የደረሰበትን አምስተኛው ትውልድ ወይም 5ጂ ፈጣን የኢንተርኔት አገልግሎት አዲስ አበባ ውስጥ በተመረጡ አምስት ሥፍራዎች ላይ አስጀመረ። አገልግሎቱ የአገርን እድገት በቴክኖሎጂ ለማገዝ ታልሞ የተጀመረ መሆኑን ኩባንያው አስታውቋል። 64 ሚሊዮን ደንበኞች እንዳሉት የገለፀው ኢትዮ ቴሌኮም ይህ የአምስተኛው ትውልድ ፈጣን የኢንተርኔት አገልግሎት በአገሪቱ ከዚህ በፊት ከተዘረጋው የኢንተርኔት አገልግሎት በ ሃያ እጥፍ ፍጥነት የሚልቅና በጤና፣ በግብርና፣ በማእድን ፍለጋ እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች ላይ ፈጣን፣ ወጪ እና ጊዜ ቆጣቢ አገልግሎቶችን ለመስጠት ያስችላል ተብሏል። ይሄው አገልግሎት በቀጣይ አንድ ዓመት ውስጥ በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች በስፋት እንዲዘረጋ ይደረጋልም ተብሏል። የቴሌኮም ኩበንያው ደንበኞች በበኩላቸው ኢትዮ ቴሌኮም ዓለም ላይ ያለውን የመጨረሻው ዘመናዊ የኢንተርኔት አገልግሎት ከማስጀመር ባሻገር በጥራትና በተደራሽነት እንዲዘምንም ጠይቀዋል።
ሰለሞን ሙጬ
አዜብ ታደሰ
ማንተጋፍቶት ስለሺ