አደጋ የገጠመዉ የተፈጥሮ ደን
ማክሰኞ፣ የካቲት 15 2003ማስታወቂያ
ለእርሻ ልማት በሚል ለአንድ (Vendata Harvests PLC.)ለተባለ የህንድ ኩባንያ የተሰጠዉ በተፈጥሮ ደን የተሸፈነዉ 3012 ሄክታር መሬት የአካባቢዉን ኗሪዎችና የአካባቢ ተፈጥሮ ተቆርቋሪዎችን እያነጋገረ ነዉ። ህይወታቸዉ ከደኑ ጋ የተቆራኘዉ የአካባቢዉ ኗሪዎች ለረዥም ዓመታት ለተፈጥሮ ክብካቤ በመሟገት ረገድ ስማቸዉ ለሚጠራዉ ለኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ ፕሬዝደንት አቤቱታቸዉን አሰምተዋል። ፕሬዝደንቱም ስጋታቸዉን ለሚመለከተዉ አካል በመጥቀስ መፍትሄ እንዲያፈላልግ አሳስበዋል። በተጠቀሰዉ ስፍራ የልማት ተግባር ለማከናወን የተሰማራዉ የህንድ ኩባንያ የተፈጥሮ ደኑን መንጥሮ የሻይ ተክል ለመትከል መዘጋጀቱ ነዉ የተገለጸዉ። ባለሙያዎች የሻይ ተክልን ለማልማት በስፍራዉ የሚገኘዉ ደን ፈፅሞ መመንጠር እንዳለበት፤ የቡና ተክል ቢሆን ግን ቢያንስ ለጥላ ሲባል ከፊሉ የደን አካል ሊተርፍ ይችል እንደነበር ያስረዳሉ። ከሶስት በመቶ በታች የተፈጥሮ ደን ሽፋኗን ማጣቷ በሚነገርላት አገር ተከታዩን ጉዳት ያላገናዘበዉ ይህን መሰሉ ተግባር ጉዳቱ ሊያመዝን ይችላል ሲሉም ያሳስባሉ።
ሸዋዬ ለገሠ
ሂሩት መለሠ