“አንድ ደብተር ለአንድ ልጅ „
ዓርብ፣ ነሐሴ 9 2006ኢትዮጵያ ውስጥ መስከረም ጠብቶ ትምህርት ቤቶች ሊከፈቱ ጥቂት ሳምንታት ብቻ ናቸው የቀሩት ፤ ስለሆነም “አንድ ደብተር ለአንድ ልጅ „የሚለውን መፈክር ይዘው የተንቀሳቀሱት ወጣቶች አላማቸውን ከግብ ለማድረስ እየተጣደፉ ይገኛሉ። የ 23 ዓመቷ ማህደር ቴድሮስ «ሐበሻ ሮትራክት ክለብ» የተሰኘው የበጎ ፍቃደኞች ስብስብ የዘንድሮው ዓመት ሊቀመንበር ናት።የመጨረሻ ዓመት የህክምና ተማሪ የሆነችው ማህደር እንደገለፀችልን ክለቡ ለተማሪዎች ደብተር ከመለገስ በተጨማሪ ሌሎች ድጋፎችንም ይሰጣል።
በቃሉ ከበደ ደግሞ ባለፈው ዓመት ደብተር እና መፃፊያ ካገኙ ተማሪዎች አንዱ ነው። የ6ኛ ክፍል ተማሪው በቃሉ የእናቱ በህይወት አለመኖር ብቻ ሳይሆን አዲሱ ዓመት ሲጀምር በምኑ እንደሚማር ያሳስበዋል። ለሚመጣው አመት ደብተር ስለማግኘቱ አያውቅም ነገር ግን ባለ ሙሉ ተስፋ ነው። በሌላ በኩል ጎረቤቱ ኤሊያስ ገብረማርያም እነዚህን ደብተሮች ከሚያሰባስቡት በጎ ፍቃደኞች አንዱ ነው። የ27 አመቱ ወጣት «ሜክሲኮ አምደ መፅሀፍት» የተባለ የመፅሀፍ መደብር አዲስ አበባ ውስጥ አለው። መደብሩ ላይ በለጠፈው “አንድ ደብተር ለአንድ ልጅ „መፈክር የተነሳ፤ ስለ አላማቸው ለሰዎች ያስረዳል። ፍቃደኛ የሆኑ ሰዎችም በቀላሉ እንዲተባበሩ ኤሊያስ እና አብረውት የሚሰሩት ደብተሮቹን የሚያሰባስቡበት መላ ፈጥረዋል።
የነማህደር እና ኤርሚያስ ዓላማ ከተሳካ በቅርቡ 10 000 ለሚሆኑ የአዲስ አበባ ተማሪዎች የመማሪያ ደብተሮችን ክለቡ ያስረክባል። ነገር ግን አንደኛ ክበቡ ካለው የአባል ቁጥር አነስተኛነት የተነሳ በመቀጠል አባላቱ በበጎ ፍቃደኝነት የሚሰሩት ስራ ከመሆኑ አንፃር የደብተር ማሰባሰቡ በክፍለ ሀገር ደረጃ ሳይሆን በዛው አዲስ አበባ እንደተወሰነ ሊቀ መንበሯ ገልፃልናለች።
መስከረም ከመጥባቱ በፊት “አንድ ደብተር ለአንድ ልጅ „በሚል መፈክር ለተቸገሩ እና አቅማቸው ለማይፈቅድ 10 000 ተማሪዎች ደብተር በማሰባሰብ ላይ ካሉት በጎ አድራጊ ወጣቶች ሁለቱን በዛሬው የወጣቶች ዓለም አነጋግረናል። ከድምፅ ዘገባው ታገኙታላችሁ።
ልደት አበበ
ተክሌ የኃላ