«አተትን» የመከላከል ጥረት
ማክሰኞ፣ ሰኔ 7 2008የዓለም የጤና ድርጅት አንድ ሰዉ ሦስቴ እና ከዚያ በላይ በቀን ቀጭን ሰገራ የሚጸዳዳ ከሆነ በተቅማጥ በሽታ መያዙን ያመለክታል። በእንዲህ ያለ ሁኔታ ቀናት ካለፈም የሰዉነቱን ፈሳሽ እያጣ እንደሚሄድ እና ያም ምናልባት ሕይወቱን ሊያሰጋዉ እንደሚችልም ያሳስባል።
በአዲስ አበባ እና በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የተከሰተዉን የአጣዳፊ ተቅማጥ እና ትዉከት በሽታ ለመቆጣጠር ከፍተኛ ሥራ እየተሠራ መሆኑ ይነገራል። የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በፌስ ቡክ ገጹ ላይ ስለበሽታዉ መንስኤ፤ ማለትም በንጽሕና ጉድለት ተከስቶ የሚተላለፍ በሽታ መሆኑን በመጠቆም ሰዎች ዉኃ አፍልተዉና አቀዝቅዘዉ፤ በዉኃ ማከሚያ የታከመ ዉኃን እንዲጠጡ፤ ምግብን በሚገባ አብስለዉ እንዲመገቡና የመመገቢያ ዕቃዎችን ንጽሕና እንዲጠብቁ፤ ከምንም በላይ ደግሞ የመጸዳጃ ቤት ንጽህናን በአግባቡ መጠበቅ እንደሚገባ፤ እጅን ከመጸዳጃ ቤት መልስ፣ ምግብ ከማሰናዳት በፊት፣ እንዲሁም ምግብ ከማቅረብ እና ከመመገብ መፊት በሳሙና በሚገባ መታጠብ እንደሚያስፈልግ መክሮ፤ ስለበሽታዉ የበለጠ ለማወቅ እና መረጃ ለማግኘት በእነዚህ ስልክ መስመሮች ደዉሉ ብሎ የስልክ ቁጥሮችን አስቀምጧል። አስገራሚዉ ነገር አንዳቸዉም የስልክ መስመሮች አይጠሩም፤ ከጠሩም አይነሱም። የሕዝብ ግንኙነት ተጠሪዎቹም ሆኑ እንዲህ ያሉ ነገሮች ሲከሰቱ መረጃ የመስጠት ኃላፊነት እንዳለዉ የሚገለጸዉ የኢትዮጵያ የኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩትንም አግኝቶ መረጃ ለማግኘት አዳጋች ሆኖ ነዉ ያገኘነዉ። ከዶቼ ቬለ የፌስ ቡክ ተከታታይና ተሳታፊዎች አንዱ የሆኑት ራቢ ሮባ ጃርሶ በአዲስአበባብቻአይደለም!! በኦሮሚያክልልበባሌዞንደሎመናወርዳምአተትገብቶሰዎችእየሞቱነው፡እስቲደውሉና አጣሩሲሉ በሰጡን ጥቆማ መሠረት ወደኦሮሚያ ጤና ቢሮ ደወልን። ይህን በተመለከተ በቂ ማብራሪያ ሊሰጡ ይችላሉ የተባሉትን ከኦሮሚያ ጤና ቢሮ የአስቸኳይ የኅብረተሰብ ጤና ችግሮች አስተዳደር አቶ ገመቹ ሹሚን አገኘን።
የዓለም የጤና ድርጅት መረጃ እንደሚያመለክተዉ ከ5 ዓመት በታች የሆኑ ሕፃናትን ሕይወት ከሚቀጥፉ ግንባር ቀደም በሽታዎች አንዱ የተቅማጥ በሽታ ነዉ። በየዓመቱም በዚሁ ምክንያት በመላዉ ዓለም የ760 ሺህ ገደማ ሕፃናት ሕይወት በዚሁ ምክንያት ይቀጠፋል። በየዓመቱም 1,7 ቢሊየን ሕፃናት በበሽታዉ ይይዛሉ። ይህን በሽታ ለመከላከል ዋናዉ መፍትሄ ንጽሕናዉ የተጠበቀ ዉኃን መጠጣት፤ የግልና የአካባቢ ንጽሕናን በአግባቡ መጠበቅ መሆኑንም በአፅንኦት ይመክራል።
ሸዋዬ ለገሠ