አርቲስት ደበበ እሸቱና ትያትር
ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 7 2008
72ኛ ዓመቱን እንደያዘ የነገረን አርቲስት ደበበ እሸቱ ወደ ሰሜን አሜሪካ ያቀናዉ ሽልማት ለመቀበል ሳይሆን ዩኤስ አሜሪካ ሎሳንጀለስ ዉስጥ በሚገኝ አንድ ዩንቨርስቲ ባዘጋጀዉ ዓለም አቀፍ አፍሪቃ ትያትር ስብሰባ ላይ ስለ አፍሪቃ ትያትር ብሎም ስለ ኢትዮጵያ ትያትር ጉዳይ መሪ ተናጋሪ ሆኖ በመጋበዝ ነበር። በዛሬዉ መሰናዶአችን ከትያትር ጋር ተጫጭቶ ትዳር ከመሠረተ ከ 50 ዓመት በላይ እንደሆነ የነገረንን ተወዳጁን አርቲስት ደበበ እሸቱን ይዘን የአፍሪቃ ብሎም የኢትዮጵያን ትያትርን ከአንጋፋዉ አርቲስት ጋር እናያለን።
በእስራኤል አገር በተሰራውና “ቀያይ ቀምቦጦች” የሚል መጠርያ በተባለዉ ፊልም ላይ መሪ ተዋናይ ሆኖ ባሳየው ልዩ የሞያ ብቃት በካናዳ ቫንኮቨር በተካሄደው “The Golden Leopard award” ሽልማት ሥነ-ስርዓት ላይ በምርጥ መሪ ትወና ዘርፍ አሸናፊ ሆኖ መሸለሙ በተለያዩ ብዙኃን መገናኛዎች ተዘግቦል። የተወነበት ፊልሙም ጀርመንን ጨምሮ በተለያዩ የአዉሮጳ ሃገራት ብሎም በሰሜን አሜሪካና አዉስትራልያ ታይቶአል። አርቲስት ደበበ እሸቱ ወደ በሰሜን አሜሪካ ካሊፎርንያ ግዛት በሚገኝ አንድ ዩንቨርስቲ ዉስጥ ስለ አፍሪቃ ትያትር ብሎም ስለ ኢትዮጵያ የትያትር መድረክ ሥራ ገለፃ ለማድረግ በዋና ተጋባዥነት ተጠርቼ ወደዝያ ሄድኩ እንጂ ፤ ካናዳ ዉስጥ ይህን ያህል ሽልማት እንደተዘጋጀለኝ ያወኩት ነገር አልነበረም ሲል ነበር ያጫወተን። በዚህ በሎሳንጀለስ በተደረገዉ ዓለም አቀፍ የአፍሪቃ ትያትር ስብሰባም ለ12 ቀናት እንደዘለቀም አጫዉቶናል።
ስዊድን ስቶክሆልም ላይ በሚካሄደዉ የፊልም ፊስቲቫል ላይ በክብር እንግድነት ተጋበዞ ከመጭዉ የካቲት 15 እስከ የካቲት 26 ቀን ድረስ በስቶክሆልሙ የፊልም ፊስቲቫል መድረክ ላይ ቃለ ምልልስ እንደሚሰጠን የነገረንን አርቲስት ደበበ እሸቱን ከድንቅ መድረክ ሥራዎቹ ጋር ረጅም ጤናና እድሜን እየተመኘን ሥለ ሰጠን ቃለ ምልልስ በዶይቼ ቬለ ስም በማመስገን ሙሉ መሰናዶዉን እንዲያደምጡ እንጋብዛለን።
አዜብ ታደሰ
ሂሩት መለሰ