ተቃዉሞ ሠልፍ በባሕርዳር ከተማ
ሐሙስ፣ ሚያዝያ 24 2011ዛሬ በባህር ዳር የክልሉን ገዥ ፓር የሚነቅፍ ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ በባህር ዳር ተካሂዷል፡፡ የአማራዴሞክራሲዊ ፓርተ ስለጉዳዩ አስተያየት እንዲሰጥ ሙከራ ቢደረግም ስብሰባ ላይ ናቸው ስለተባለ አልተሳካም። ባሕር ዳር በአንድ ሳምንት ውስጥ የተለያዩ ዓላማዎችን ያነገቡ ሶስት ሰላማዊ ሰልፎችን አስተናግዳለች፡፡ ባለፈው ሳምንት በከተማዋ የሚገኙ የአራት ሆስፒታል የህክምና ባለሙያዎች ከጥቅማጥቀም ጋር በተያያዘ ሰልፍ አድርገዋል፣ የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ደግሞ ህወታችን አደጋ ላይ ነው መንግስት ጥበቃ ያድርግልን ሲሉ ሰልፍ አካሂደዋል፤ዛሬ ደግሞ በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶችና ሌሎችም የህብረተሰብ ክፍሎች በአማራ ተወላጆች ላይ እየደረሰ ያለውን ስደት፣ መፈናቀልና ሞት የክልሉ ገዥ ፓርቲ ማሰቆም አልቻለም፣ አማራንም መወከል አይችልም ከስልጣን ይውረድ፣ የክልሉን ሰላም ማስጠበቅ ተስኖታልና ሌሎችንም መፈክሮች ሲያሰሙ ነው ያረፈዱት፡፡
ከሰልፉ አስተባባሪዎች መካከል አቶ እንዳልካቸው ክንዴ የሰልፉ ዓላማ ዓላማዎች፣ ሰሞኑን በተለያዩ አካባቢዎች አማራ ላይ አነጣትረው ግድያ የፈፀሙ ሰዎች ለፍርድ እንዲቀርቡ፣ አዴፓ ሰምና ርዕሰ መስተዳድር ከመቀየር ውቺ ያደረገው የመዋቅር ለውጥ ስለሌለ ያን መቃወምና የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር አምቦ ላይ ያደረጉት ንግግር አማራን ያስከፋ በመሆኑ ይቅርታ እንዲጠይቁ አሊያም ከስልታን እንዲወርዱ ለማሳሰብ መሆኑን ተናግሯል፡፡
ሌላዋ የሰልፉ አስተባባሪ ትህትና በላይ እንደምትለው ደግሞ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ በክልሉ ተወላጆች ላይ የሚደርሰውን ጭፍጨፋ እንዲያስቆም ለመጠየቅና ያ ካልሆነ ግን የሚችሉት መንገድ ሁሉ ተጠቅመው ህዝቡን ከጥቃት ለመታደግ የተዘጋጀ ሰልፍ መሆኑን አብራርታለች፡፡ ሌላው የሰልፉ ተሳታፊ አቶ አድነው መኳንንት እንዳለው አማራ ርስቱን የተቀማ በመሆኑ ይህን ለማሰማትና የአማራን ጥቃትና ውርደት ለመከላከል ሰልፉ የመጀመሪያ ማሳያ ነው ብሏል፡፡
ተመሳሳይ ይዘት ላቸው ሰልፎች በደብረታቦር፣ በጎንደርና በምስራቅ ጎጃም የተለያዩ የወረዳ ከተሞች መካሄዳቸውን የየዞን የህዝብ ግንኙነት ባለሙያዎች አረጋግጠውልናል።
በጉዳዩ ዙሪያ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲን አመራሮች፣ የመስተዳድሩን ኃላፊዎች ሀሳብ ለማካትት ያደረግሁት ጥረት ጎንደር ላይ ስብሰባ ናቸው በሚል አልተሳካልኝም።
ዓለምነው መኮንን
ማንተጋፍቶትስ ስለሺ
እሸቴ በቀለ