ባልተለመደ አካባቢ ሞዴልነትን እያስተዋወቀ ያለው ወጣት
ዓርብ፣ ሰኔ 21 2016ስራውን ለመጀመር ድፍረት ይጠይቃል
የህይወት መንገድ ለየቅል ናት ። አንዳንዱ የህይወቱን መንገድ ሳያገኛት እንዲሁ ሲባዝን ዘመኑን ሊጨርስ ይችላል ። አንዳንዱ ደግሞ በለስ ቀንቶት ገና በለጋ ዕድሜው ከዕኩዮቹም ቀድሞ መንገዱን ያገኝና በስኬት ያሳርጋል። ስራ በዘመኑ ቋንቋ ቢዝነስ ያበላል ወይስ አያበላም በሆነበት በዚህ ዘመን ነገን ተስፋ አድርገው ሌሎች ያልሞከሩትን ስራ የሚጀምሩት ደግሞ ለእነርሱ ህልምን ለመኖር ጅምር ይሆንላቸዋል። ጤና ይስጥልን አድማጮቻችን በዛሬው የወጣቶች ዓለም ዝግጅታችን ከመዲናዪቱ አዲስ አበባ ከ360 በላይ ኪሎ ሜትሮች ርቃ በምትገኘው የጅማ ከተማ የሞዴሊንግ ትምህርት ቤት ከፍቶ በርቀት ምክንያት ተፈጥሮ የለገሰቻቸውን ዉበት እና ማንነት አጉልተው ለማውጣት የሚታትሩ ወጣቶችን ስለሚያስተምር የአንድ ወጣት ተሞክሮ ይዘንላችሁ ቀርበናል።
ትውልድ እና ዕድገት
አዲሱ ደመቀ ይባላል ። ትውልድ እና ዕድገቱ በጂማ ዞን ማና ወረዳ ነው ። እንደማንኛውም የአካባቢው ወጣት የመጀመሪያ እና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በማና እና በጅማ ከተማ ተከታትሏል። በኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ውስጥ ሞያተኛ ሆኖም አገልግሏል። የህይወት መንገዷ እና መዳረሻዋ ብዙ መሆኑን የተረዳው አዲሱ እንዲሁ ተቀጣሪ ሆኖ መቆየት አልፈለገም ። የተለያዩ ሞያዎችን ሞካክሯል። የካሜራ ባለሞያ ሆኖ ሰርቷል፤ በራዲዮ የስፖርት ኮሚታተርነትም እንዲሁ ሞክሯል ። አሁን ደግሞ ምናልባትም በእጁ ከያዘውም በላይ ነገን ተስፋ የሚያደርግበት አንድ ስራ ጀምሯል። ብዙዎች እንኳንስ ከመዲናዪቱ ርቀው ይቅር እና እዚያም ሆነው ሊሞክሩት የማይፈቅዱትን የሞዴሊንግ ስልጠና ትምህርት ቤት በጅማ ከተማ ከፍቶ ጥቂት የማይባሉ ወጣቶችን በማስተማር ላይ ይገኛል። አዲሱ በአንድ ወቅት በድንገት ለዚያውም በጉዞ ላይ ከተዋወቀው ሰው ያገኘው መረጃ እንዴት ይሆን ቀልቡን የሳበው ?
ወደ ስራው የገባበት አጋጣሚ
«በሆነ ሰዓት ወደ አዲስ አበባ እየሄድኩ በመኪና ውስጥ የተዋወቋኳት ልጅ ነበረች ። ስለሞዴሊንግ ግንዛቤ የሰጠችኝ ፤ እኔም ፍላጎቱ ነበረኝ ፤ ቁመቴ 1 ሜትር ከ82 ሴንቲ ሜትር ነበር ። በዚህ ምክንያት ወደ ትምህርት ቤት በቀጥታ መግባት እንዳለብኝ ወሰንኩ ፤ ልጅቷን አማከርኩ ነገረችኝ ፤ ከዚያ ጅማ ውስጥ እንደዚህ አይነት ትምህርት ቤት እንዲኖር እና ይህን መንገድ መከተል አለበት ብዬ አሰብኩ ፤ ከዚያም ተማርኩ ፤ ስልጠና ወስጄም ጅማ ላይ ትምህርት ቤቱን ከፈትኩ»
ኃይማኖታዊ እና ሌሎች ባህላዊ ተጽዕኖዎች በወጣቶች የአለባበስም ሆነ ሁለንተናዊ ስብዕና ላይ ብርቱ ተጽዕኖ በሚያሳድርበት ማህበረሰብ ውስጥ ዉበት ፣ ፋሽን ፣ አለባበስ እና ሌሎች በራስ መተማመንን ለማጎልበት የሚያግዝ ትምህርት መስጠት ምን ያህል ፈታኝ እንደሚሆን አይጠረጠርም። በዚህ ሁኔታ ውስጥ ግን ተፈጥሯዊ ተክለ ቁመና እና ዉበት ፣ የአነጋገር ለዛ እና ሞዴል ሊያደርጉ የሚችሉ ሌሎች ተፈጥሯዊ ስጦታዎችን ታድለው ነገር ግን በስልጠና እጦት ወይም መራቅ ህልማቸውጋ ሳይደርሱ ለቀሩት መድረስ ደግሞ በእርግጥ በራሱ ልዩ ትርጉም ይኖረዋል። ለመሆኑ አዲሱ በጅማ ከተማ በከፈተው በዚህ የሞዴሊንግ ትምህርት ቤት ምን ያህል ወጣቶች እያሰለጠነ ይሆን ?
ምን ያህል ተማሪዎችን እያስተማረ ይሆን ?
«160 ተማሪዎች የደረሱበት ጊዜ ነበር አምና ፤ ያው ሲመረቁ ሁሉም ሄዱ ፤ ስራ አግኝተው አዲስ አበባ የገቡ ልጆች አሉ ፤ እዚህም በባህል እና ቱሪዝም ቢሮ ውስጥ እየሰሩ ያሉ ልጆች አሉ ። አሁን ግን 60 ያህል ልጆች በጥራት አንድ ዓመት የሞላቸው ልጆች አሉ ፤ ስድስት ወር የደረሱ ልጆች አሉ ፤ ጥሩ ስራ እየሰራን እንገኛለን »
ህልማቸውን ለመኖር በቅርበት ያገኙት ዕድል
ሞዴል ፌሬወይኒ ገብረማሪያም ትባላለች። አዲሱ ደመቀ በከፈተው የሞዴሊንግ ትምህርት ቤት ተማሪ ናት ። ሞዴል የመሆን በውስጧ የቆየ ፍላጎት በአንድ አጋጣሚ በሰማችው ማስታወቂያ ተስባ እንደመጣች ትናገራለች።
« ፍላጎቱ ነበረኝ ፤ ነገር ግን ጅማ ውስጥ እንዳለ አላወቅኩም ነበር ፤ ከዚያ ማሳታወቂያ ሰማሁ ለምን አትመዘገቡም የሚል ሃሳብም ይቀርብልን ነበር ፤ ከጓደኞቼ ጋር ሄደን ተመዘገብን በዚያው ቀጠልን»
እንደፍሬወይኒ ሁሉ ናታኒ ተስፋዬም አዲሱ ደመቀ በከፈተው የኤቢ የሞዴሊንግ ትምህርት ቤት ሰልጣኝ ተማሪ ነው ። ለእርሱ ሞዴልነት የህይወት መዳረሻ ህልሙ ነው ። ህልሙን ለመጨበጥ በአቅራቢያ ካገኘው ትምህርት ቤት ደርሷል።
« ህልሙ ነበረኝ ያው አንድ ተማሪ ሞዴሊንግ ለመማር ብዙ መስፈርቶች ቢኖሩትም ሞዴል ለመሆን ከ1 ሜትር ከ83 በላይ ነኝ ፤ ያ ነገር እና እንደገና ደግሞ ትልቅ ፍላጎቱ ስላለኝ እና ህልሜም ስለነበር ነው»
ፍሬወይኒም ሆነች ናታኒ በአቅራቢያ ባገኙት የሞዴሊንግ ትምህርት ቤት ተገቢውን ስልጠና ወስደው ከአካባቢያቸው አልፈው እስከ ዓለማቀፍ የሚሻገር ሞዴል የመሆን ህልም አላቸው ያንኑ ከማሳካት ወደ ኋላ እንደማይሉም ነው የሚናገሩት ።
ተማሪዎቹ ከስልጠና በኋላ ምን ያስባሉ ?
«እኔ መጨረሻዬ ሁል ጊዜ ፋሽንን ፕሮሞት ማድረግ እፈልጋለሁ ፤ እናም ደግሞ የተሻለ ዕድል መጥቶ ሀገራችንን ማስተዋወቅ እፈልጋለሁ »
« እኔ እንኳ ሃሳቤ ከኢትዮጵያ የመውጣት ሃሳብ ነው ያለኝ ፤ በዚህ በሞዴሊንጉ ማለት ነው፤ እና ለዚያ ደግሞ አብዛኛውን ሮል ሞዴል የማደርጋቸው አሉ። ሶሻል ሚዲያ ላይ የምከታተላቸው እነ ዮሐንስ አስፋው እና እነ አቤል አሉ ። ፈጣሪ ካለ ገና ጀማሪም ስለሆንኩ ሁሉን ነገር ከጨረስኩ በዚያ ፕሮፌሽናል በሆነ ነገር የመስራት ትልቅ ህልም አለኝ »
በውጣ ውረድ የተሞላ ተግዳሮት
ዛሬ ዛሬ የትኛውም የስራ መስክ የአዋጭነት ጥናት ሳይጠና አይገባበትም ። በማህበረሰቡ ውስጥም የተለመደው ይኸው ነው ፤ አንዱ ሲሰራ አይተው ስኬታማ ከሆነ የእርሱን መንገድ መከተል አልያም በብዙ ቦታዎች አዋጭ ናቸው ተብለው በሚታሰቡ የስራ መስኮች ላይ መሰማራት። ብዙዎች ያልሞከሩትን ብቻም አይደለም ለማሰብ እንኳ ዕድል የማይሰጥ እንዲህ እንደ አዲሱ አይነት የስራ መስክን መርጦ መጀመር የተለየ ያደርጋል ። ለመሆኑ አዲሱ ይህን ስራ አንድ ብሎ ሲጀምር የገጠመው ተግዳሮት ይኖር ይሆን ? ኪራይ የሚከፍለው አጥቶ የጉልበት ስራ እስከመስራት አድርሶት እንደነበር ይናገራል።
«ተግዳሮት በጣም ነበረብኝ፤ ብቸኝነት እስኪሰማኝ ድረስ ማለት ነው፤ የሆነ ጊዜ ስራዬን ለእይታ ባበቃሁ ጊዜ ልብስ ለብሳ የወጣችን ልጅ እንዲህ አይነት ልብስ ለብሳ መውጣት የለባትም ብለው በጸጥታ አካላት ተይዣለሁ ፤ በፋይናንስም ቢሆን ሜዳ ላይ እስከማሰራት የደረስኩበት ጊዜ ነበር፤ የጉልበት ስራ ሰርቼ የቤት ኪራይ እስከመክፈልም ደርሻለሁ ። »
ቀጣዩ ዕቅዱ ምን ይሆን ?
እውነት ነው ። እንኳንስ ሌላው የማይደፍረውን ለዚያውም የማህበረሰቡ ኃያማኖታዊ እና ባህላዊ ተጽዖኖ በበረታበት አካባቢ ይቅር እና በታዳጊ ሀገር ዉስጥ ብዙም የማይሞከረውን የስራ መስክ መሞከር በራሱ የሚያስመሰግን ተግባር ነው። አዲሱ በውጣ ውረድ ውስጥ ሆኖም ነገን ለመጨበጥ ዛሬ መታተሩን ገፍቶበታል። ለመሆኑ ቀጣይ ምን የመስራት ዕቅድ ይኖርህ ይሆን ስንል ጠይቀነው ነበር ።
«ጅማን ማስተዋወቅ ፣ የኦሮሚያ ክልል ባህል ዓለማቀፍ ማድረግ፤ የጅማ ከተማ አሁን እያደገች ነው በዚህ ላይ ሞዴሎች የሚወጡባት ከተማ የማድረግ እና እያስተዋወቁ መቀጠል እፈልጋለሁ ፤ ተማሪዎቼ ከኢትዮጵያም አልፈው በአፍሪቃ ደረጃ እንዲታወቁልኝ እፈልጋለሁ»
በአውሮፕላንና ድሮን ፈጠራ ላይ የተሰማራው ወጣት
የወጣቱ ጥረት በእርግጥ ይበል የሚያሰኝ ነው፤ የማህበረሰቡን ትውፊት ሳይለቁ ፤ ባህላዊ አልባሳቱንም በዘመናዊ አሰራር ፋሽን እንዲሆኑ እና ሲለበሱ የሚያምሩ መሆኑን ለማሳየት ጥረት እያደረገ ነው ። ይህ ጥረት በዕውቀት ሲደገፍ በዚህ መስክ ትልቅ ቦታ መድረስ ለሚሹ ወጣቶች እዚያው በቅርባቸው በተፈጠረላቸው ዕድል የህልማቸውን መንገድ አንድ ብለው እንዲጀምሩም ዕድል ፈጥሮላቸዋል።
ታምራት ዲንሳ
ነጋሽ መሐመድ