በጋምቤላ የውኃ መጥለቅለቅ ከ10 ሺሕ በላይ ሰዎች አፈናቀለ
ሰኞ፣ ሐምሌ 19 2013በጋምቤላ ክልል ኑዌር ዞን በተከሰተ ጎርፍ በርካታ ነዋሪዎች መፈናቀላቸውን በዞኑ የላሬ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ። ተፈናቃዮች በበኩላቸው በውሀ ተከብበው ያለምንም እርዳታ እንደሚገኙ ተናግረዋል። የክልሉ አደጋ መከላከል መስሪያ ቤት እርዳታ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ እንደሆነ ለዶይቼ ቬለ ገልጧል፡፡
ከሐምሌ አጋማሽ ጀምሮ በአካባቢው እየጣለ ባለው ዝናብ ምክንያት ጂካዎ የተባለው ወንዝ ሞልቶ አካባቢውን አጥለቅልቋል፡፡ የወንዙ ሙላት ሜዳማ የሆነውን የአካባቢውን መሬት በከፍተኛ ሁኔታ በማጥለቅለቁ ነዋሪዎች ለከፋ ጉዳት መጋለጣቸውን ነዋሪዎች ለዶቼ ቬለ በስልክ አመልክተዋል፡፡ የ6 ልጆች እናት የሆኑት ወ/ሮ ኛካችና ሌላዋ አንድ እናት በውሀተከብበው ይገኛሉ ድጋፍም አላገኙም፡፡
እድል ቀንቷቸው ተፈናቅለው በአንድ ትምህርት ቤት ከሚገኙት ተፈናቃዮች መካከል አቶ ጋሏክ ሪችና አቶ ቦል ዴንግ የምግብ ችግር እንዳለባቸው ጎርፉም እንስሳቱን ጨምሮ ለአደጋ እንዳጋለጣቸው አመልክተዋል፡፡
በጋምቤላ ክልል ኑዌር ዞን የላሬ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ጋትዊች ቤል ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ ጎርፉ በፈጠረው ችግር በወረዳው 5 ቀበሌዎች ከ10ሺህ 200 በላይ ሰዎች ተፈናቅለዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ በጎርፉ በርካታ ቤቶች መጥለቅለቃቸውን፣ 5000 ሄክታር የሚጠጋ ማሳ ላይ ያለ ቦቆሎ በውሀ መዋጡንም ተናግረዋል፣ በቂ እርዳታም አልተደረገምም ብለዋል፡፡
የጋምቤላ ክልል አደጋ መከላከልና ዝግጁነት መስሪያ ቤት ኃላፎ አቶ ጋትቤል ሙን የተጠናቀቀ ሪፖርት ባይደርሳቸውም ለተጎዱ ሰዎች እርዳታ ለማድረስ ከእርዳታ ሰጪ ድርጅቶች ጋር እየተነጋገሩ እንደሆነ አመልክተዋል፡፡ የጋምቤላ ክልል ተፈጥሯዊ አቀማመጥ በአብዛኘው ሜዳማ በመሆኑ ብዙ አካባቢዎች በየኣመቱ በውሀ ሙላት ይጥለቀለቃሉ፡፡
ዓለምነው መኮንን
ሸዋዬ ለገሰ