በየመን የኢትዮጵያውን ስደተኞች ሥቃይ
ረቡዕ፣ መጋቢት 26 2004ከለላ ይደረግላቸው ዘንድ በመዲናይቱ ሰንዓ በተጠለሉበት ዩ ኤን ኤች ሲ አር በር ላይ በተደጋጋሚ ጥቃት ደረሰባቸው። የጄዳ ወኪላችን ነቢዩ ሲራክ በስልክ ያነጋገራቸው እነዚሁ ስደተኞች በየመን የፀጥታ ኃይላት የተቀነባበረ ጥቃት እንደደረሰባቸውና ከተመድ የስደተኞች ጉዳይ ተመልካች መሥሪያ ቤት UNHCR ርዳታ እንዳልተደረገላቸው ገልጸውለታል።
----------------------------------------
ይሁንና፣ የመን የሚገኙ የኢትዮጵያ ተገን ጠያቂዎች በየመን የደህንነት ኃይሎች ጥቃት እንደደረሰባቸዉና ከUNHCR ርዳታ እንዳላገኙ ቢያስታውቁም የመን የሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን በምህፃሩ UNHCR ወቀሳዉን አስተባብሏል። የመን የሚገኙ የኢትዮጵያ ተገን ጠያቂዎች በየመን የደህንነት ኃይሎች ጥቃት እንደደረሰባቸዉ ቢያስታውቁም የመን የሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን በምህፃሩ UNHCR ወቀሳዉን አስተባብሏል።
በየመን የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን በምህፃሩ UNHCR እውቅና የሰጣቸው የኢትዮጵያ ተገን ጠያቂዎች በየመን ሰላም አስከባሪ ኃይላት ስለደረሰባቸው የድብደባ እና ሌሎች ጥቃቶች ቢገልፁም የመን UNHCR ቃል አቀባይ ዘይድ አል-አላያ ይህንን ያስተባብላሉ።
« በፍፁም በፍፁም ምንም ዓይነት የደረሰ ጥቃት የለም። የተወሰኑ ተገን ጠያቂዎች ወደ UNHCR ህንፃ በስተጀርባ መተው ነበር። ወደ ሌላ ቦታ መስፈር ይፈልጋሉ። ይህ ግን በአሁኑ ጊዜ ከባድ ነው። ምክንያቱም የመን የምትቀበለው ከጥቂት አገሮች ለሚመጡ ስደተኞች ነውና ። እነዚህ ተገን ጠያቂዎች ከየመን UNHCR ጋ ስምምነት በመፍጠር ወደ ተዘጋጀላቸው መጠለያ ተወስደዋል። መጠለያዉ በደቡብ የመን የሚገኝ ነዉ። ተገን ጠያቂዎቹ በራሳቸው ፍቃድ በአውቶቢስ ተጭነው ነዉ ወደ መጠለያው የተወሰዱት። በአጠቃላይ ስደተኞቹ ምንም አይነት ጥቃት አልደረሰባቸውም። ስለ ተገን ጠያቂዎች ወቀሳ የቀረበው በየመን እና ከየመን ውጪ በሚገኙ የመገናኛ ብዙኋን ነው።»
ቃል አቀባዩ የሚስማሙበት አንድ ነገር ቢኖር ስደተኞቹ UNHCR ወደ አዘጋጀው ካርታስ ወደተባለው ትልቅ እና ሰፊ መጠለያ መወሰዳችን ብቻ ነው። UNHCR ለተገን ጠያቂዎቹ የበኩሉንም ርዳታ እየሰጠ ይገኛል ሲሉም ይገልፃሉ።
« ከለላ እንሰጣለን። ለተገን ጠያቂዎች አስፈላጊ የሆኑ የህይወት አድን ርዳታ እናደርጋለን። መጠለያ እንሰጣለን። የአካል ጉዳተኛ ለሆኑት ርዳታ እንጣለን ሠርተዉ ራሳቸዉን መርዳት ለማይችሉት ደግሞ የገንዘብ ድጋፍ እንሰጣለን። »
ይሁንና በርካታ ስደተኞች ከዚህ ቀደም ስለተከሰቱ ችግሮች ላነሱት ጥያቄና በቂ መተዳደሪያ እንዲሰጣቸውም አመልክተዉ ምላሽ አላገኙም። የየመን UNHCR ቃል አቀባይ ዘይድ አል-አላያ እንደሚሉት አንዱ ችግር የተገን ጠያቂዎች በየመን መንግስት እውቅና ማግኘቱ ላይ ነው።
« ሶማሊያውያን ወደ የመን ሲመጡ በተገን ጠያቂነት የመን እውቅና ሰጥታቸዋለች። ይህም የሆነው የመን በ19 51 እና በ1967 ስምምነት ተፈራርማለች። ነገር ግን ሌሎች ዜጎች፤ እንደ ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ያሉት ተገን ጠያቂዎች ግን ወደስደተኛ ሁኔታ መወሰኛ አካል መሄድ አለባቸው። ምክንያቱም UNHCR በአጠቃላይ ለስደተኞች እና ለተገን ጠያቂዎች ከለላ አይሰጥም።»
ነቢዩ ሲራክ
አርያም ተክሌ
ልደት አበበ
ሸዋዬ ለገሰ