1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በኮንሶ ዞን  የተባባሰው ጥቃት 

ሰኞ፣ መጋቢት 26 2014

የአካባቢው ነዋሪዎች  እንዳሉት ጥቃቱ የተደራጁ በተባሉ ኃይሎች እየተፈፀመ የሚገኘው በወረዳው ገርጪ፣ ዱገያና ሰገን ገነት በተባሉ የገጠር ቀበሌያት ውስጥ ነው፡፡ አንድ የዓይን እማኝ ጥቃት አድራሾቹ ከባለፈው ዓርብ ጀምሮ ቀበሌያቱን በመውረር አሁን ድረስ መኖሪያ ቤቶች እያቃጠሉ ይገኛሉ ሲሉ ለዶቼ ቬሌ DW  በስልክ ገልፀዋል ፡፡

https://p.dw.com/p/49RiL
Äthiopien Heimkehrer aus Konso

በኮንሶ ዞን  የተባባሰው ጥቃት 

በደቡብ ክልል ኮንሶ ዞን በነዋሪዎች ላይ የሚደርሰው ጥቃት እየተባባሰ መምጣቱን የአካባቢው ነዋሪዎች ተናገሩ።ጥቃትና ግጭቱ እየተባባሰ የመጣው በዞኑ ሰገን ዙሪያ ወረዳ ባለፈው ዓርብ ምሽት እሥረኞችን ለማስፈታት በወረዳው ፖሊስ ጣቢያ ላይ ቦንቦች ከተወረወሩ በኋላ ነው፡፡መረጃዎች እንደሚጠቁሙት በወረዳው በሚገኙ አራት ቀበሌዎች አሁን ድረስ ሰዎች እየተገደሉ ፣ በብዙ መቶዎች የሚቆጥሩ የመኖሪያ ቤቶችም እየተቃጠሉ ነው ፡፡
የአካባቢው ነዋሪዎች  እንዳሉት ጥቃቱ የተደራጁ በተባሉ ሀይሎች እየተፈፀመ የሚገኘው በወረዳው ገርጪ፣ ዱገያና ሰገን ገነት በተባሉ የገጠር ቀበሌያት ውስጥ ነው፡፡
በጥቃቱ ከገረጪ ቀበሌ ሸሽተው ማምለጣቸውን የሚናገሩት አንድ የአይን እማኝ ጥቃት አድራሾቹ ከባለፈው ዓርብ ጀምሮ ቀበሌያቱን በመውረር አሁን ድረስ መኖሪያ ቤቶች እያቃጠሉ ይገኛሉ ሲሉ ለዶቼ ቬሌ DW  በስልክ ገልፀዋል ፡፡
ዶቼቬሌ DW በጥቃቱ ዙሪያ ያነጋገራቸው የኮንሶ ዞን የመንግሥት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች መመሪያ ሃላፊ አቶ ሠራዊት ዲባባ ትንኮሳና ጥቃቱ ቀደም ሲልም የነበረ ቢሆንም የተባባሰው ግን እሳቸው ፀረ ሰላም ያሏቸው ሀይሎች ባለፈው ዓርብ ለሊት በሰገን ዙሪያ ወረደ ፖሊስ ጣቢያ ላይ ቦንብ በመወርወር እስረኞችን ለማስፈታት ያደረጉት ሙከራ መክሸፉን ተከትሎ ነው ብለዋል፡፡
የኮንሶ ዞን አጎራባች ከሆነው የደራሼ ልዩ ወረዳ የተነሱ ያሏቸው ሀይሎች  በቀበሌያቱ በሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ጥቃት ማድረሳቸውን ገልፀዋል፡፡
ታጣቂዎቹ እስከአሁን በሰወ ሕይወትና ንብረት ላይ ስላደረሱት የጉዳት መጠን የተጠየቁት የመምሪያው ሃላፊው መጠኑን እስከአሁን ማወቅ አልተቻለም ፣ በቀጣይ አጣርተን የምናሳውቅ ይሆናል ብለዋል፡፡
የደቡብ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የክልሉ ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ሀላፊ አቶ አለማየሁ ባውዴ ዛሬ በግጭቱ ዙሪያ በሰጡት መግለጫ በአካባቢው ጥቃቱን እያደረሱ የሚኙት በደራሼ ልዩ ወረዳ ውስጥ የሚንቀሳቀሱና የደራሼ ዞን እንመሰርታለን የሚሉ ቡድኖች የፈጠሩት ነው ብለዋል፡፡
ጥቃቱን ለማስቆም የክልሉ መንግሥት ከሕብረተሰቡ ጋር ከመምከር  ጎን ለጎን የፀጥታ ተቋማት በጋራ እየሠሩ ይገኛሉ ብለዋል፡፡
ዶቼ ቬሌ DW በጉዳዩ ላይ ያነጋገራቸው የታጠቁ ሀይሎች  ይንቀሳቀሱበታል የተባለውን የደራሼ ልዩ ወረዳን አስተደደርን ለማነጋገር ያደረገው ሙከራ የልዩ ወረዳው ዋና አስተዳዳሪ ከደቂቃዎች በኋላ ደውሉልኝ ባሉት መሠረት ሲደወልላቸው ጥሪ ባለመመለሳቸው አስተያየታቸውን ማካተት አልተቻለም ፡፡


ሸዋንግዛው ወጋየሁ
ኂሩት መለሰ
ሸዋዬ ለገሠ