በኬንያ ያሉ ሶማልያውያን ስደተኞችን ለመመለስ መታሰቡ
ቅዳሜ፣ ኅዳር 7 2006
«ዩ ኤን ኤች ሲ አር» ስምምነቱን ከተፈራረመ ከአንድ ቀን በኋላ ባወጣው ማስጠንቀቂያ፣ በዳዳብ እና በካኩማ መጠለያ ጣቢያዎች የሚኖሩትን ስደተኞችቹን የመመለሱ ተግባር በፈቃደኝነታቸዉ ላይ የተመሠረተ መሆን እንዳለበት አመልክቶዋል። በተፈረመው ስምምነት መሠረት፣ ስደተኞቹን በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት ወደ ሶማልያ የመመለስ ዕቅድ ተይዞዋል።
የኬንያ መንግሥት ይህን ያደረገው በናይሮቢዉ ዌስት ጌት የገበያ ማዕከል ዉስጥ የ68 ሰዎች ሕይወት ያጠፋው ዓይነት የአክራሪ ሙሥሊሞች ጥቃት እንዳይደገም ቅድመ ጥንቃቄ ለማድረግ መሆኑን አመልክቶዋል፣ ጥቃቱን ተከትሎ የኬንያ መንግሥት ባለሥልጣናት በሰጡት የተለያየ መግለጫ በዳዳብ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ ውስጥ የአክራሪው ሙሥሊሞች ቡድን አሸባብ ደጋፊዎች እንዳሉ በማመልከት፣ ጣቢያው እንዲዘጋ ሲጠይቁ ተሰምቶዋል።
ስደተኞቹን ለመመለስ የተደረሰውን ስምምነት በአሁኑ ጊዜ ተግባራዊ ለማድረግ በሶማልያ ሁኔታው ምቹ መሆኑን በበርሊን የጀርመናውያኑ ዓለም አቀፍ ፀጥታ ጉዲዮች ተመልካች ተቋም የአፍሪቃ እና የመካከለኛው ምሥራቅ ተንታኝ ወይዘሮ አኔተ ቬበር ይጠራጠሩታል።
« የመመለሱ ተግባር በፈቃደኝነት ላይ የተመረኮዘ ነው። የሶማልያ ስደተኞች በርግጥ ወደ ትውልድ ሀገራቸው መመለስ መፈለግ አለመፈለጋቸውን ራሳቸው መወሰን አለባቸው። በኔ አስተያየት ፣ በውጭ የሚኖሩ ሶማልያውያን በወቅቱ በሀገራቸው ተመልሰው ሊኖሩ የሚችሉበት ብዙ አስተማማኝ ቦታ የለም። እርግጥ፣ ኬንያውያኑ ስደተኞቹ ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ማግባባት እንደሚችሉ ተስፋ አድርገዋል። ይሁንና፣ በሶማልያ ያለው ሁኔታ ተመላሾችን ለመቀበል የሚያመች ሆኖ አላየውም። »
ከ20 ዓመት በላይ ምሥቅልቅል ሁኔታ እና የርስበርስ ጦርነት የተካሄደባት ሶማልያ፣ በተለይም ሞቃዲሾ፣ የአፍሪቃ ህብረት ሰላም አስከባሪ ጓድ ከተሠማራ ወዲህ መጠነኛ መረጋጋት ይታይባታል። እርግጥ፣ እአአ ከ2012 ዓም ወዲህ ሀገሪቱ ሕጋዊ ፕሬዚደንት ቢኖራትም፣ መንግሥታዊ መዋቅሮች ገና አሁን ነው እየተገነቡ ያሉት። እና ሁኔታዎች ጋና ባልተመቻቹበት ወቅት ስደተኞቹ በራሳቸው ፍላጎት ይመለሳሉ መባሉ አጠያያቂ ነው፣ እንደ አኔተ ቬበር ግምት፣
« ሂደቱን በጥንቃቄ መከታተል ይገባል። የመመለሱን ተግባር የሚያመቻቸው «ዩ ኤን ኤች ሲ አር » ነው። ስለዚህ ጉዳዩ እነሱንም በከፊል ይመለከታል። ስደተኞቹን የሚመልስ አንድ ኮሚሽን የተቋቋመ ሲሆን፣ ሂደቱ በሦስት ዓመታት ውስጥ መጠናቀቅ አለበት። በዚሁ ሂደት ወቅት አጀብ ሊደረግላቸው ይገባል፣ በፈቃደኝነትም ነው የሚፈፀመው፣ ማለትም፣ ስደተኞች የሚመለሱት ፈቃደኞች ሲሆኑ ብቻ ነው። ይህን አሰራር ከተከተልን ስደተኞች ችግር አይኖራቸውም። ወደ ትውልድ ሀገርህ ለመመለስ ስምምነት መፈራረም አያስፈልግህም። ይሁን እንጂ፣ የመመለሱ ሂደት በፈቃደኝነት ሳይሆን ብግዳጅ የሚደረግ ከሆን አደገኛ ሊሆን ይችላል። » የመመለስ ችግር የለባቸውም። »
ብዙ ኬንያውያን በሀገራቸው የሚኖረው ስደተኛ ቁጥር ከፍ ማለቱ ፈታኝ ሁኔታ ከመፈጠሩ ጎን የፀጥታ ስጋት ሊደቅን ይችላል ባይ ናቸው። በዚህም የተነሳ አሁን የሀገራቸው እና የሶማልያ መንግሥት ስደተኞቹን በ«ዩ ኤን ኤች ሲ አር » አመቻቺነት ወደሶማልያ ለመመለስ መስማማታቸውን በደስታ ተቀብለውታል። ለደህንነታቸው ሲሉ ወደ ኬንያ የሸሹት ስደተኞች የፀጥታ ስጋት ደቀኑ በሚል የተሰማውን አባባል አኔተ ቬበር አይጋሩትም።
« የሶማልያ ስደተኞች በብዛት ኬንያ መግባታቸው የሚታወቅ ነው፣ አዲስ ነገር አይደለም። ባዳዳብ እና በካኩማ መጠለያ ጣቢያ ከሚኖሩት መካከል ብዙዎቹ ለችግር የተጋለጡ ናቸው። እና እነዚህን ስደተኞች ከፀጥታ ስጋት ጋ ማገናኘቱ ሊገባኝ አልቻለም። እ,አa በ2012 ዓም የኬንያ መንግሥት በሀገሩ ያሉ የሶማልያ ስደተኞች በጠቅላላ በአንድ የመጠለያ ጣቢያ ውስጥ እንዲሰባሰቡ ትዖeዛዝ አስተላልፎ ነበር፤ ግን ከሕዝቡ ብርቱ ተቃውሞ ስለገጠመው መንግሥት ትዕዛዙን ወዲያው ነበር የሸረው። በመጠለያ ጣቢያዎቹ ውስጥ ያሉት ችግረኞቹ ስደተኞች የአሁን ፀጥታ ስጋታ ናቸው መባሉ ፖለቲካዊ ምክንያት ያለው መስሎ ይታየኛል። »
ዜና ምንጭ ሮይተርስ ስምምነቱን አስመልክቶ ባወጣው ዘገባ መሠረት፣ የሶማልያ መንግሥት እና የተመደ ተመላሾቹ ስደተኞች በሀገር መልሶ ግንባታው እንዲሳተፉ የሚያስችላቸው አንድ የመልሶ ማዋሀድ መርሀግብር ለመጀመር አቅደዋል።
አርያም ተክሌ
ልደት አበበ