በኦስትሪያ ሀገር ጓብኚዎች ላይ የተጣለ ጥቃት
ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 30 2005ወደ ሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ የተጓዙት አስር የኦስትሪያ ዜጎች አላማ መዝናናት ነበር። በአባይ ወንዝ ላይ መቅዘፍ። ይሁንና ከነዚህ አገር ጎብኚዎች መካከል አንዱ ማንነታቸው ባልታወቁ ሰዎች እሁድ ማለዳ የመገደል መጥፎ ዕጣ ገጥሞታል ። እንደ የኦስትሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተጠሪ ማርቲን ቫይስ ገለጻ የግድያው መንስኤ በጎብኚዎቹ ላይ የታቀደ ዘረፋ ነው። «አራት አባል ያለው የኦስትሪያ ቡድን በጀልባ ላይ ሆኖ ከቅዳሜ እስከ እሁድ አጥቢያ በስፍራው አድሮ ነበር። እሁድ ጠዋት ሰው ሊዘርፋቸው ሞከረ ጀልባቸውንም አወደመ። በዚህ ዝርፍያ ጊዜም ተኩስ ተከፎቶ አንድ ኦስትሪያዊ ሊገደል ችሏል።»
በግድያው ስንት ሰዎች እንደተሳተፉ እና ማን እንደፈፀመው እስካሁን በውል የታወቀ ነገር የለም። የኦስትሪያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገዳዮቹ ሀገር ጎብኚዎችን ለመዝረፍ ያለሙ መሆናቸውን በርግጠኝነት ቢገልጽም የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ የግዲያው መንስኤ እስካሁን አልተረጋገጠም ነው ያሉት።
ባለፈው ዓመት ኢትዮጵያን ከኤርትራ ጋር የሚያዋስነዉን አካባቢ ይጎበኙ የነበሩ አንድ ኦስትሪያዊን ጨምሮ አምስት አዉሮጳዉያን በታጣቂዎች ተገድለዉ፥ ሌሎች ታግተዉ እንደነበር ይታወሳል። የኦስትሪያ ዉጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ከዚያ ጊዜ ወዲህ ዜጎቹ ወደ ኢትዮጵያ ጠረፍ እንዳይጓዙ ቢያስጠነቅቅም ወደ ሌሎች የኢትዮጵያ ግዛቶች እንዳይጓዙ ግን አልከለከለም። አምሳደር ዲና ሙፍቲ እንደገለፁትም የሰሞኑ አደጋ የተካሄደበት አካባቢ የተረጋጋና ሰላማዊ ነው። »
ጥቃት ወይም አደጋ በሚደርስበት ጊዜ መንግሥታቸው ለተጎጂዎቹ ምን አይነት ርዳታ ያደርጋል? በወቅቱ ከኢትዮጵያ መንግስት ትብብር አግኝተው እንደሆን የኦስትሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተጠሪን ማርቲን ቫይስን ጠይቄያቸዋለሁ።
«አዎ። ሶስቱ ከጥቃቱ የተረፉት በአንድ ዋሻ ውስጥ በመሸሸግ ሊያመልጡ ችለዋል። ኋላም በያዙት የሳተላይት ስልክ አዲስ አበባ ወደሚገኘው የኦስትሪያ ኤምባሲ ደውለው አሳወቁ። ኤምባሲውም በበኩሉ ስለሁኔታው የኢትዮጵያን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አሳወቀ። ያኔ የኢትዮጵያ መንግስት እነዚህ የኦስትሪያ ዜጎችን የሚፈልጉ ፖሊስ እና ጦር ኃይል በመላክ በሕይወት የተረፉትን እና የሟአቹን አስክሬን ጭምር ወደ አዲስ አበባ ሊወስዱ ችለዋል። »
እንደ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ገለፃ የሟች አስክሬን በአዲስ አበባ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ይገኛል። የቀሩት ዘጠኝ አገር ጎብኚዎችስ በምን ሁኔታ ላይ ይገኛሉ?
« ስድስቱ በጥቃቱ ወቅት አብረው ያልነበሩት ስለተፈጠረው ሁኔታ ምንም አላወቁም ነበር። ሶስቱ ዝርፍያና ግድያው ሲካሄድ አብረው የነበሩት ግን እጅጉን ተዳክመው ነበር። አንዳችም የአካል ጉዳት ግን አልደረሰባቸውም። በአሁኑ ጊዜ በደህና አዲስ አበባ ገብተዋል። »
ልደት አበበ
አርያም ተክሌ