በኢትዮጵያ ግጭት ዙሪያ የጀርመን አቋም
ማክሰኞ፣ ኅዳር 14 2014
ጀርመን በሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት ምክንያት በሀገሪቱ የምታከናውነውን የልማትና የዕርዳታ ትብብር እንደማታቋርጥ ገለፀች። የጀርመን የኢኮኖሚ ትብብርና የልማት ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ዩርገን ሃርት ለዶይቼ ቨለ "DW" እንዳስታወቁት በግጭቱ መስፋፋት ምክንያት በረሃብና በድህነት ስቃይ ውስጥ የሚገኘው ሕዝብ ቁጥር በአሳዛኝ ሁኔታ በእጅጉ አሻቅቧል።በመሆኑም የጀርመን የኢኮኖሚ ትብብርና የልማት ሚኒስቴር ከለጋሽ ሃገራትና ከአውሮጳ ህብረት ጋር በመቀናጀት በሃገሪቱ የጀመረውን የልማት ትብብር የሚቀጥል ይሆናል ብለዋል። ጀርመን መንግሥት የጀመረውን ለውጥ ተከትሎ የ 100 ሚልዮን ዩሮ የልማት ትብብር በጀት መድባ የነበረ ቢሆንም ገንዘቡ ሙሉ ለሙሉ የሚለቀቀው የትግራዩ ግጭት ፖለቲካዊ መፍትሄና ዕልባት ሲያገኝ መሆኑንም ነው ያስረዱት። እስከዛው ግጭቱ ከተስፋፋባቸው ከትግራይ አማራና አፋር ክልሎች ውጪ ባሉ አካባቢዎች የልማትና የዕርዳታ እንቅስቃሴው እንደሚቀጥል ታውቋል። የጀርመኑ ነጻ ዲሞክራቶቹ ፓርቲ FDP የልማት ጉዳዮች ፖለቲከኛው ኦላፍ ኢን ዴር ቤክ በበኩላቸው በኢትዮጵያ ለልማትና ዕርዳታ የሚወለው ገንዘብ በቀጥታ ለኢትዮጵያ መንግሥት ለተፋላሚ ኃይላትና በቀጠናው የግጭቱ ተዋናይ ለሆኑ አካላት እንዳይደርስ በሚገባ ክትትልና ቁጥጥር እናደርጋለን ሲሉ ገልፀዋል። ጀርመን በኢትዮጵያ ሰላም ለማስፈን በሚደረገው ጥረት ከተፋላሚ ኃይላቱና ከአፍሪቃ አህጉራዊው ሕብረት ጥቃቄ ሲቀርብላት ብቻ የበኩላን ሚና እንደምትጫወትም ይፋ አድረገዋል። የዶይቼ ቬለዉ ዳንኤል ፔልዝ ያጠናቀረዉን ዘገባ የፍራንክፈርቱ ወኪላችን እንዳልካቸው ፈቃደ ተርጉሞታል።
እንዳልካቸው ፈቃደ /ዳንኤል ፔልዝ
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ