1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በአማራ ክልል የተደነገገው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅና የሕግ ባለሞያ አስተያየት

ዓርብ፣ ሐምሌ 28 2015

የሕገ መንግሥትና ሕገ መንግሥታዊ ጉዳዮች መምህሩ አቶ አሮን ደጎል በክልሎች ጠያቂነት ችግሮች ከአቅም በላይ ናቸው ተብሎ ሲጠየቅ እና የፌዴራል መንግሥቱ እገዛ ሲያስፈልግ፣ በሁለተኛ ደረጃ የፌዴራል መንግሥቱ ያለ ክልሎች ፈቃድ የክልል መንግሥታት ሰላምና ሕግን ማስከበር አልቻሉም ብሎ ሲያምን በራሱ ተነሳሽነት ጣልቃ ገብቶ ሕግና ሥርዓትን ያስከብራል።

https://p.dw.com/p/4UnVb
Äthiopien Notstände in Amhara
ምስል DW/J. Jeffrey

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅና የሕግ ባለሞያ አስተያየት

ትናንት በክልሉ ርእሠ መስተዳድር ተፈርሞ የወጣ መሆኑ የተነገረለት ደብዳቤ በክልሉ ያጋጠመውን የፀጥታ መደፍረስ በመደበኛ የሕግ ማስከበር ሥርዓት ለመቆጣጠር አዳጋች ሆኖ በመገኘቱ የፌደራል መንግስት ጣልቃ እንዲገባ ይጠይቃል። የሚኒስትሮች ምክር ቤት ዛሬ ባደረገው ውይይት በአማራ ክልል "የሚታየውን በትጥቅ የተደገፈ" ያለውን  እንቅስቃሴ በመደበኛ የሕግ ማስክበር ሥርዓት ለመቆጣጠር ወደ ማይቻልበት ደረጃ የተሸጋገረ በመሆኑ፣ ይህም "የክልሉን ነዋሪ አጠቃላይ የኢኮኖሚ እና የማህበራዊ እንቅስቃሴ በከፍተኛ ደረጃ ያወከ እና ሕገ መንግስዝታዊ ሥርዓቱን አደጋ ላይ የጣለ በመሆኑ፣ የሕዝብን ሠላምና ፀጥታ ለማስጠበቅ የአስቸኳይ ጉዜ አዋጁ ተደንግጓል" ብሏል።
በጉዳዩ ላይ ያነጋገርናቸው የሕግ ባለሙያ የፌዴራል መንግሥት ክልሎች እገዛ ሲጠይቁ እና በራሱ የክልሎችን ፈቃድ ሳይጠብቅ ሰላምና መረጋጋት ለማስፈን በክልሎች ጣልቃ እንዲገባ ሕገ መንግሥት እንደሚፈቅድለት እና "ጊዜያዊ አስተዳደር እስከመትከል፣ የአስፈፃሚነትን ሚና ለጊዚያዊነትም እስከመረከብ የሚደርስ" ሥልጣን እንደተሰጠውም ገልፀዋል።በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች ዛሬም በመከላከያ ሠራዊት አባላት እና በፋኖ መካከል ውጊያ መኖሩን ነዋሪዎች ገልፀዋል።

በአማራ ክልል የተከሰተው የፀጥታ መናጋት "በክልሉ ከፍተኛ ሰብዓዊ፣ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ኪሳራ እያደረሰ" መሆኑን ጠቅሴ በክልሉ ርእሠ መስተዳድር ፊርማ የተጠየቀ ደብዳቤ የፌደራል መንግሥት ከመደበኛው የሕግ ማስከበር ሥርዓት ባሻገር ወደ ክልሉ ጣልቃ እንዲገባና ሕግና ሥርዓትን እንዲያስከብር ይጠይቃል። ይህን በአማራ ክልል እየተካሄደ ያለውን "በትጥቅ የተደገፈ ሕገወጥ" ያለው እንቅስቃሴ በመደበኛ የሕግ ማስከበር ሥርዓት ለመቆጣጠር ወደ ማይቻልበት ደረጃ መሸጋገሩን የገለፀው የሚኒስትሮች ምክር በክልሉ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ዛሬ ደንግጓል።የሚኒስትሮች ምክር ቤት በአማራ ክልል ያለውን የትጥቅ እንቅስቃሴ የክልሉን ነዋሪ አጠቃላይ የኢኮኖሚ እና የማህበራዊ እንቅስቃሴ በከፍተኛ ደረጃ ያወከ እና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን አደጋ ላይ የጣለ ነው ብሎታል።
የፌዴራል መንግሥት በሁለት መንገድ ሰላምና ፀጥታን ለማስከበር ወደ ክልሎች ጣልቃ ይገባል ያሉት የሕገ መንግሥት እና ሕገ መንግሥታዊ ጉዳዮች መምህሩ አቶ አሮን ደጎል በክልሎች ጠያቂነት ችግሮች ከአቅም በላይ ናቸው ተብሎ ሲጠየቅ እና የፌዴራል መንግሥቱ እገዛ ሲያስፈልግ፣ በሁለተኛ ደረጃ የፌዴራል መንግሥቱ ያለ ክልሎች ፈቃድ የክልል መንግሥታት ሰላምና ሕግን ማስከበር አልቻሉም ብሎ ሲያምን በራሱ ተነሳሽነት ጣልቃ ገብቶ ሕግና ሥርዓትን ያስከብራል። ብለዋል። ከእነዚህ የሕገ መንግሥት ድንጋጌዎች በተጨማሪ የፌዴራሉ መንግሥት በክልሎች ጣልቃ የሚገባበትን ሥርዓት ለመደንገግ በወጣ አዋጅ ተጨማሪ ሥልጣን ተሰጥቶታል ብለዋል።

የአማራ ክልል ርእሠ መስተዳድር የፌዴራል መንግሥት ጣልቃ እንዲገባ የጠየቁበት ደብዳቤ ወጥቶ ከመዘዋወሩ በፊት መከላከያ ሠራዊት ከፋኖ ጋር በክልሉ ግጭት ውስጥ ገብቶ የነበረ መሆኑ ብዙዎች የሕጋዊ አካሄድ ጥያቄ እንዲያነሰምሱ አድርጓል። የሕግ ባለሙያው እንደሚለት ግን የፌዴራል መንግሥቱ ክልሎችን ሳይጠይቅ ጣልቃ በመግባት ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን ማድረግ የሚያስችለው ሥልጣን በአዋጅ እንደተሰጠው በመግለጽ ከጥቂት አመታት በፊት በሶማሌ ክልል ያለ ክልሉ ፈቃድ የተደረገውን የፌዴራል መንግሥቱን ጣልቃ ገብነት አስታውሰዋል።ክልሎች የፌዴራል መንግሥት ጣልቃ ገብቶ ሕግና ሥርዓት እንዲያስከብር ፈቃድ ከሰጡ በኋላ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የመደንገጉ ኃላፊነት ሙሉ በሙሉ የፌዴራል መንግሥቱ መሆኑንም ተናግረዋል። 

የሚኒስትሮች ምክር ቤት አማራ ክልል ውስጥ ተከስቷል ያለው ችግር በሀገር ደህንነት እና በሕዝብ ሰላም ላይ የደቀነው አደጋ ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ መምጣቱን አስታውቋል።በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት መሠረት እአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሥራ ላይ ባለ ጊዜ የታወጀ ከሆነ በታወጀ በአርባ ስምንት ሰዓታት ውስጥ ለምክር ቤቱ መቅረብ እንዳለበት የተደነገገ ሲሆን ምክር ቤቱ እንዳሁኑ በሥራ ላይ ባልሆነበት ወቅት የሚታወጅ ከሆነ ግን በታወጀ በአሥራ አምሥት ቀናት ውስጥ መቅረብ እንዳለበት ይደነግጋል። ለዚህ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መደንገግ ምክንያት የሆነው ውጊያ እና የትጥቅ ግጭት ዛሬም በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች መቀጠሉን ነዋሪዎች ገልፀዋል።
ሰሎሞን ሙጬ
ኂሩት መለሰ
ሸዋዬ ለገሠ