በምስራቅ አፍሪቃ ስጋት የደቀነዉ የአንበጣ መንጋ
ዓርብ፣ ሚያዝያ 2 2012ማስታወቂያ
የበረሃ አንበጣ መንጋ አሁንም በኢትዮጵያ፣ ኬንያ እና ሶማሊያ አሳሳቢ መሆኑን የዓለም የእርሻና የምግብ ድርጅት አስጠነቀቀ። የአንበጣ መንጋው በበረታባቸው ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ሶማሊያ፣ደቡብ ሱዳን፣ዩጋንዳና ታንዛኒያ 20 ሚሊዮን ሰዎች እንዲሁም በየመን 15 ሚሊዮን ሰዎች ብርቱ የምግብ ዋስትና እጦት እንደገጠማቸው ገልጿል።
በመጋቢት ወር የሚጠበቀው ዝናብ በመጪዎቹ ወራት በምሥራቅ አፍሪቃ ከፍተኛ የአንበጣ መንጋ እንደሚከሰት የገለጸው ድርጅቱ ከኬንያ ወደ ደቡብ ሱዳን እና ዩጋንዳ እንደሚዛመት አስጠንቅቋል። ከምሥራቅ አፍሪቃ በተጨማሪ አዳዲስ የአንበጣ መንጋ እየተፈለፈለ በሚገኝባቸው በኢራን እና በየመን አሳሳቢ እንደሚሆን የዓለም የእርሻና የምግብ ድርጅት በትናንትናው ዕለት ያወጣው መግለጫ ይጠቁማል። ድርጅቱ እንዳለው በኮሮና ሳቢያ በአገራቱ በሰዎች እና አስፈላጊ ቁሳቁሶች እንቅስቃሴ ላይ ገደብ መጣሉ የአንበጣ መንጋን ለመከላከል ፈተና ሆኗል። የአማራ ክልል ግብርና ልማት ቢሮ የሰብል ባለሙያ አቶ አለባቸው አሊጋዝ በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች አንበጣ መታየቱን ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል።
እሸቴ በቀለ
አዜብ ታደሰ