በማዕከላዊ ኢትዮጵያ የግሪሳ ወፍ ያሳደረው ሥጋ
ሐሙስ፣ ጥቅምት 8 2016ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የተከሰተው የግሪሳ ወፍ በደረሱ ሰብሎች ላይ ሥጋት መፍጠሩን የአካባቢው አርሶአደሮች ለዶቼ ቬለ ገለጹ ፡፡ በክልሉ የስልጤ ፣ የሀላባ እና የሃድያ ዞን አርሶ አደሮች እንዳሉት ካለፉት ሁለት ሳምንታት ወዲህ በዞኖች የተከሰተው የግሪሳ ወፍ በደረሱ የስንዴ ፣ የማሽላ እና የዳጉሳ ሰብሎች ላይ ጉዳት እያደረሰ ይገኛል ፡፡ የግብርና ቢሮ በበኩሉ ወደ ዞኖቹ የገባውን የወፍ መንጋ ለመከላከል በባህላዊ መንገድና በአይሮፕላን የመድሃኒት ርጭት በማከናወን ጉዳቱን ለመቀነስ እየጣረ እንደሚገኝ አስታውቋል ፡፡
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልልየተከሰተው የግሪሳ ወፍ በደረሱ ሰብሎች ላይ ሥጋት መፍጠሩን የአካባቢው አርሶአደሮች ለዶቼ ቬለ ገለጹ ፡፡ በክልል የስልጤ ፣ የሀላባ እና የሃድያ ዞን አርሶአደሮች እንዳሉት የወፍ መንጋው በአካባቢው መታየት የጀመረው ከባለፉት ሁለት ሳምንታት ወዲህ ነው ፡፡
በዞኖቹ አብዛኞቹ ወረዳዎች ውስጥ የታየው መንጋ በሰብል እርሻዎቻቸው ላይ ጉዳት እያደረሰ እንደሚገኝ አርሶአደሮቹ ተናግረዋል ፡፡ መንጋው በተለይ የስንዴ ፣ የማሽላ እና የዳጉሳ ሰብሎችን እየበላ እንደሚገኝ ነው የሀላባና የስልጤ ዞን አርሶአደሮች ለዶቼ ቬለ የገለጹት ፡፡
ዶቼ ቬለ በአርሶአደሮቹ ሥጋት ዙሪያ ያነጋገራቸው የአርባምንጭ እፅዋት ጥበቃ ክሊኒክ ኃላፊ አቶ ሙሉዓለም መርሻ ሰሞኑን መነሻውን ኬኒያ እና የኢትዮጵያ የስምጥ ሸለቆ አካባቢዎች ያደረገ የወፍ መንጋ ወደ ክልሉ መግባቱን አረጋግጠዋል ፡፡ አንድ ነጠላ የወፍ መንጋ አባል በቀን እስከ አምስት ግራም አህል የመብላት አቅም እንዳለውና በሰብል ምርት ላይ ሊያደርስ የሚችለው ጉዳት ያዛኑ ያህል ሰፊ መሆኑን ተናግረዋል ፡፡
መንጋውን ሙሉ በሙሉ መጥፋት አስቸጋሪ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ሙሉዓለም ነገር ግን አሁን ላይ የጉዳት መጠኑን ለመቀነስ በባህላዊ መንገድና እንዲሁም ከፌዴራል ግብርና ሚንስቴር ጋር በመተባበር የአይሮፕላን የመድሃኒት ርጭት በመከናወን ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል ፡፡
ታላቁ የምሥራቅ አፍሪካ ስምጥ ሸለቆ በሚያቋርጠው የደቡብ ኢትዮጵያ አካባቢ ለግሪሳ ወፍ ፣ ለአንበጣ መንጋ እና ለተምች ወረርሽኝ የተጋለጠ ሥለመሆኑ የዘርፉ ባለሙያዎች ይናገራሉ ፡፡
ሸዋንግዛው ወጋየሁ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
አዜብ ታደሠ