በሙስሊም ሃገራት ተቃውሞና ውግዘት፣
ሰኞ፣ መስከረም 7 2005በዩናይትድ እስቴትስ ፤ ካሊፎርኒያ ውስጥ የተሠራው ፣ የነቢዩ መሐመድን ክብር የሚነካ መሆኑ የተነገረለት ፊልም ፤ በ «ዩ ቲዩብ » በአደባባይ ለእይታ በኢንተርኔት መረብ ከተለቀቀ በኋላ፤ በዐረቡ ዓለምና በእስላማዊ አገሮች የቀሰቀሰው ብርቱ ተቃውሞ፤የበረደ አይመስልም። ባለፈው ሳምንት ፣ ቤንጋዚ ፤ ሊቢያ ውስጥ የአሜሪካ አምባሰደርና 3 አሜሪካውያን ረዳቶቻቸው ከተገደሉ ወዲህ ፣50 ያህል ተጠርጣሪዎች ተይዘዋል። በተለያዩ አገሮች የሚታየው የተቃውሞ ሰልፍ እንደቀጠለ ሲሆን ፣ ስለመፍትኄውም መታሰቡ አልቀረም። ነብዩ መሐመድን አዋርዷል በተባለ ፊልም ምክንያት በሙስሊም ሃገራት የሚካሄደው ተቃውሞ ዛሬም ቀጥሎ ውሏል ። ዛሬ በአፍጋኒስታንና በ ኢንዶኔዥያ በተካሄዱ የተቃውሞ ሰልፎች የአሜሪካን ባንዲራ የተቃጠለ ሲሆን ሰልፈኞችም ሞት ለአሜሪካ በማለት ተቃውሞአቸውን ሲያስሙ ነበር ። የኢንዶኔዢያ ፖሊስ በመዲናይቱ ጃካርታ በሚገኘው የአሜሪካን ኡምባሲ ፊት ለፊት ተሰብሰበው የነበሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ ተቃዋሚዎችን በአስለቃሽ ጢስና በውሐ በትኗል ። በአፍጋኒስታን መዲና ካቡል ደግሞ በሺህዎች የሚቀጠሩ አደባባይ የወጡ ተቃዋሚዎች መኪናዎችና ሱቆችን ሲያቃጥሉ ፖሊስ ላይም ድንጋይ ወርውረዋል ። ደማችን እስኪፈስ ድረስ ነብያችንን እንስከብራለን ያሉት ተቃዋሚዎቹ አሜሪካን ለፈፀመችው የእጇን ታገኛለች ሲሉም ዝተዋል ። ካቡል የሚገኙ የብሪታኒያና የአሜሪካን ኤምባሲዎች በመዘጋታቸው ሰልፈኞቹ የውጭ ዜጎች መኖሪያ በሆኑ ቤቶች አካባቢ ነበር ቁጣቸውን የገለፁት ። ሊባኖስ ውስጥ ደግሞ ዛሬ ቤይሩት ውስጥ በሺህዎች የሚቆጠሩ ተቃዋሚዎች በተቃውሞ ሰልፍ ቁጣቸውን ገልፀዋል ። ኢዝላምአባድ ፓኪስታን ውስጥ ዛሬ በተካሄደ ተቃውሞ የ 2 ሰዎች ህይወት ጠፍቷል ። ትናንት በለንደንና በአውስትሬሊያ በቱርክና በፓኪስታን ሰልፎች ተካሂደዋል ። በሌላ በኩል የኢራን ባለሥልጣናት ፊልሙን አውግዘው አሜሪካን ለድርጊቱ ይቅርታ ትጠይቅ ብለዋል ።በአሁኑ ጊዜ የተቃውሞው ሰልፍ ምን እንደሚመስል ፣ ተክሌ የኋላ ዘጋቢአችንን ነቢዩ ሲራክን በስልክ አነጋግሯል።
ነብዩ ሲራክ
ተክሌ የኋላ
አርያም ተክሌ