ቀኝ አክራሪነት በጀርመን
ማክሰኞ፣ ኅዳር 11 2005
በጀርመን የቀኝ አክራሪነት አዝማሚያ ከቀድሞው እየተጠናከረ በመሄድ ላይ መሆኑን በቅርቡ ይፋ የሆነ አንድ ጥናት አስታውቋል ። እንደ ጥናቱ በተለይ በምሥራቅ ጀርመን የውጭ ዜጎች ጥላቻ ከቀድሞው አሁን ተባብሷል ። የዛሬው አውሮፓና ጀርመን ዝግጅታችን ትኩረት ነው ።
ባለፉት 12 ዓመታት ጀርመን ውስጥ በ 9 የውጭ ዜጎችና በአንድ ፖሊስ ላይ የደረሱ ግድያዎች ፣ በህቡዕ ሲንቀሳቀስ በቆየ ቀኝ አክራሪው ቡድን መፈፀሙ አነጋግሮ ሳያበቃ በቅርቡ የወጣ አንድ ጥናት በጀርመን የቀኝ አክራሪነት አስተሳሰብ አራማጆች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን መጠቆሙ አሳስቧል ። ከአንድ ሳምንት በፊት ነበር አቃቤ ህግ በ 10 ሩ ሰዎች ግድያ ከተጠረጠሩት ራሱን ብሔራዊ ሶሻሊስት ህብረት ብሎ የሚጠራው በህቡዕ የሚንቀሳቀሰው ቀኝ አክራሪ ቡድን አባላት መካከል በህይወት በምትገኘው ላይ በይፋ ክስ የመሰረተው ። በወንጀሉ አፍቃሪ ናዚዎች መጠርጠራቸው ይፋ ከወጣበት ካለፈው አመት አንስቶ በጀርመን የቀኝ አክራሪዎች ጉዳይ እንዳነጋገረ ነው ። ፍሪድሪክ ኤበርት የተባለው የጥናት ተቋም ባለፈው ሳምንት ባወጣው ዘገባ በመላ ጀርመን የቀኝ አክራሪነት አስተሳሰብ እየጨመረ መምጣቱን ማመልከቱ ጉዳዩ ይበልጥ እንዲተኮርበት አድርጓል ። የጥናቱ ውጤት እንዳመለከተው ድርጅቱ ከዛሬ 2 አመት በፊት የቀኝ አክራሪነት አዝማሚያ በጀርመን በምን ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ካካሄደው ጥናት ውጤት ጋር በማነፃፀር እንዳቀረበው ያኔ በመላ ጀርመን ከመቶ ሲሰላ 8.1 የነበረው አሁን ወደ 9 በመቶ አድጓል ። እንደ ጥናቱ ይህ አዝማሚያም ከአካባቢ አካባቢ ይለያያል ። በተለይ በምዕራብ ጀርመን ግዛቶች የዛሬ 2 አመት ይታይ የነበረው አዝማሚያ እጅግ በመጠኑ አነስተኛ መቀነስ ሲያሳይም በምሥራቁ ክፍል ግን እጅግ ከፍ ብሎ ተገኝቷል ። ከ 10.5 ወደ 15.8 አድጓል ። ይህም እንደ ተቋሙ እስካሁን በተካሄዱት ጥናቶች ከተገኘው ውጤት ከፍተኛው ነው የፍሪድሪሽ ኤበርት ጥናት ተቋሙ ባልደረባ ራልፍ ሜልትዘር በተለይ በምሥራቅ ጀርመን የቀኝ አክራሪነት ስሜት እየተስፋፋ የመጣበትን ምክንያት ከህዝቡ የኑሮ ሁኔታ ጋር ያያይዙታል ። ችግሩን መከላከል እንደሚገባም ያሳስባሉ ።« እኛ በተለይ እንደምንገምተው ከሆነ በምሥራቁ ጀርመን ፌደራል ክፍላተ ሃገር አንዳንድ ተስፋ የቆረጡ ሰዎች የሚገኙባቸው አካባቢዎች አሉ ። ይህ የሚታየው ችግርም ሆነ ይሽው ዘረኝነት በጣም ተጠናክሮ የሚንጸባረቅባቸውም እነዚሁ ናቸው ። ዴሞክራቲክ ፓርቲዎች የቀኝ አክራሪዎች አጀንዳዎች ቀስ በቀስ እየሰረጉ እንዳይገቡ በግልፅ ማከላከል አለባቸው ። በአካቢዎችን ቀበሌዎች ደረጃ በቀኝ አክራሪዎችና በዴሞክራቲክ ፓርቲዎች ፖለቲከኞች መካከል የተቀራረበ ግንኙነት የለም ። »
በጀርመን ዘረኝነትን መዋጋት አንዱ አላማው አድርጎ የሚንቀሳቀሰው ባቢሎን የተባለው ድርጅት መሪ ዶክተር መኮንን ሽፈራው በምስራቅ ጀርመን ቀኝ አክራሪነት ለመስፋፋቱ ምክንያቱ ተደጋግሞ እንደሚነሳው የሥራ አጡ ቁጥር በመጨመሩ ብቻ አይደለም ይላሉ ።
አቶ ዮናስ ለማ ጀርመን ሲኖር 27 አመቱ ነው ። ምስራቅ ጀርመን ኖሯል ። በጀርመን ዘረኝነት ጎልቶ መታየት የጀመረው ከውህደቱ በኋላ መሆኑን ይናገራል ። ሆኖም በዚህ ዘመን ዘረኝነት ጊዜ ያለፈበት አስተሳሰብ መሆኑ ሊታወቅ ይገባል ባይ ነው ። እንደ ዶክተር መኮንን ሽፈራው በጀርመን ዘረኝነትን ለመዋጋት ቁልፉ መሣሪያ ትምህርት ነው ። ይህ ውጤታማ መሆኑን የራሳቸውን ድርጅት እንቅስቃሴ በምሳሌነት በማንሳት ያስረዳሉ ።
ሂሩት መለሰ
አርያም ተክሌ